የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ተወዳጅ እና በየሳምንቱ ተናፋቂ እንዲሆን ዋንኞቹ ምክንያቶች የሚመዘገቡት ውጤቶች፣ የተጫዋቾች ክህሎትና ችሎታ እንዲሁም የሚቆጠሩ ግቦች ማራኪነት ብቻ አይደሉም።
ከአሸናፊነታቸው ጎን አሰልጣኞች በየጨዋታዎቹ ይዘው የሚገቡት ታክቲክ፣ የሚከተሉት ፍልስፍና እና እስከ መጨረሻዋ ፊሽካ ድረስ የሚጓዙበት የማይበገር የአሸናፊነት መንፈስ ዋናው ምክንያት ነው።
በዚህ መሠረት በዋንጫ ብዛት፣ በታክቲክ አብዮት እና በሊጉ ላይ ባሳረፉት ጥልቅ አሻራ የሊጉን ታሪክ የቀየሩ አስር አሰልጣኞች በእግር ኳስ ቤተሰቡ ዘንድ ልዩ ቦታ እንዳላቸው ቢቢሲ አስነብቧል።
1. ሰር አሌክስ ፈርጉሰን
ፈርጉሰን ከ1992/93 እስከ 2012/13 ድረስ 13 የፕሪሚየር ሊግ ዋንጫዎችን ከማንቸስተር ዩናይትድ ጋር አሳክተዋል። ለሁለት አስርት ዓመታት የማንቸስተር ዩናይትድን የበላይነት በማረጋገጥ በታሪክ ቁጥር አንድ አሰልጣኝ ናቸው።
ከኤሪክ ካንቶና እስከ ክርስቲያኖ ሮናልዶ፣ ከዌይን ሩኒ እስከ ካርሎስ ቴቬዝ ድረስ ፈርጉሰን የዩናይትድን ቡድን ገንብተዋል። በ13 የፕሪሚየር ሊግ ዋንጫዎችም በሊጉ ታሪክ የማይነካ ክብረወሰን ይዘው ይገኛሉ።
2. ፔፕ ጓርዲዮላ
የእንግሊዝ እግር ኳስን በአጨዋወት መንገድ ከቀየሩ አሰልጣኞች መካከል ቀዳሚው የታክቲክ አብዮተኛ ናቸው።
ከማንቸስተር ሲቲ ጋር ስድስት የፕሪሚየር ሊግ ዋንጫዎችን ያሸነፉት ጓርዲዮላ፣ በ2017/18 የ100 ነጥብ ድል በማስመዝገብ ታሪክ ሠርተዋል። ከዚያም ሲቲን በተከታታይ አራት ጊዜ የፕሪሚየር ሊግ ሻምፒዮን ያደረጉ የመጀመሪያው አሰልጣኝ ሆነዋል።
3. አርሰን ቬንገር
የእንግሊዝን እግር ኳስ ከሜዳ ላይ ታክቲክ በላይ በሆነ መልኩ የቀየሩ አሰልጣኝ ናቸው። አርሰናልን በ1998፣ 2002 እና 2004 የፕሪሚየር ሊግ ሻምፒዮን አድርገዋል።
ከሁሉም የሚለየው የ2003/04 የ“Invincibles” ዘመን ነው። አርሰናል በዚያ የውድድር ዘመን አንድም ጨዋታ ሳይሸነፍ የሊጉን ዋንጫ አንስቷል።
ቬንገር ከአሰልጣኝነታቸው በተጨማሪ የአመጋገብ እና የልምምድ ስርዓትን በማዘመን የእንግሊዝን እግር ኳስ ባሕል የለወጡ ሊቅ ናቸው።
4. ጆዜ ሞሪንሆ
“ዘ ስፔሻል ዋን” በመባል የሚታወቁት ጆዜ ሞሪንሆ በቼልሲ ሦስት የፕሪሚየር ሊግ ዋንጫዎችን አሳክተዋል።
በ2004/05 በመጀመሪያው ዓመት የፕሪሚየር ሊጉ ቆይታቸው፤ ቼልሲ በ12 ነጥቦች ልዩነት ዋንጫ ሲያነሳ ቡድኑ በ38 የሊግ ጨዋታዎች 15 ግቦች ብቻ የተቆጠሩበትን የማይደፈር የተከላካይ መስመር ገንብተዋል።
5. የርገን ክሎፕ
የሊቨርፑልን የ30 ዓመታት የዋንጫ ጥም የቆረጡ አሰልጣኝ ናቸው። በከፍተኛ ጫና እና በፈጣን ሽግግር የተገነባው የክሎፕ እግር ኳስ አጨዋወት ሊቨርፑልን በአውሮፓና በእንግሊዝ ሀያል እና አስፈሪ ቡድን አድርጎታል።
6. ክላውዲዮ ራኒየሪ
"5,000 ለ 1" የተባለውን የሌስተር ሲቲ ተአምር የመሩት ክላውዲዮ ራኒየሪ ከፕሪሚየር ሊጉ ድንቅ አሰልጣኞች መካከል ስድስተኛ ደረጃ ላይ የተቀመጡ ውጤታማ አሰልጣኝ ናቸው።
7. ኬኒ ዳግሊሽ
ከሊቨርፑል ጋር ውድድሩ ፕሪሚየር ሊግ ከመሰኘቱ በፊት ታላቅ ስኬት ያስመዘገቡ ቢሆንም፣ በብላክበርን ሮቨርስ ያነሱት የ1994/95 ዋንጫ በፕሪሚየር ሊጉ ታሪክ ልዩ ቦታ አለው።
ዳግሊሽ ብላክበርንን ከሁለተኛ ዲቪዚዮን ወደ ፕሪሚየር ሊጉ ካሳደጉ በኋላ ቡድኑን ከኃያሉ ማንቸስተር ዩናይትድ ጋር በመፎካከር ዋንጫውን አሳክተዋል። በዚህም ከሁለት የተለያዩ ክለቦች ጋር የእንግሊዝ የሊግ ዋንጫ ካሸነፉ አሰልጣኞች መካከል አራተኛው ሆነዋል።
8. ሮቤርቶ ማንቺኒ
ማንቸስተር ሲቲን ለመጀመሪያው የፕሪሚየር ሊግ ዋንጫ ያበቁ የማይረሱ አሰልጣኝ ናቸው።
የ2011/12 የውድድር ዘመን ዋንጫ በተለየ ሁኔታ የተገኘ ነበር። በመጨረሻው ሳምንት ሲቲ በጭማሪ ሰዓት ሁለት ግቦችን አስቆጥሮ የማይረሳውን የሻምፒዮንነት ድል አስመዝግቧል። የሰርጂዮ አጉዌሮ የ94ኛ ደቂቃ ግብ በፕሪሚየር ሊጉ ታሪክ ከተመዘገቡ አይረሴ ግቦች መካከል አንዱ ነው።
9. ሚኬል አርቴታ
ሚኬል አርቴታ በ2025/26 የውድድር ዘመን አርሰናልን ወደ ፕሪሚየር ሊግ ዋንጫ በመምራት ለክለቡ የረጅም ጊዜ የዋንጫ ጥበቃ ማብቂያ አበጅቷል።
ከአርሰን ቬንገር 2004 የInvincibles ዘመን በኋላ ዋንጫውን ያስገኘ የመጀመሪያው የአርሰናል አሰልጣኝም ሆኗል።
አርቴታ በተጨማሪም የሲቲ እና የሊቨርፑልን የ8 ዓመታት የበላይነት በመስበር የመጀመሪያውን የፕሪሚየር ሊግ ዋንጫ በማንሳት የፕሪሚየር ሊጉ የምንጊዜም ቁጥር ዘጠኝ አሰልጣኝ ሆኗል።
10. ካርሎ አንቼሎቲ
በቼልሲ የመጀመሪያ የፕሪሚየር ሊግ ዘመናቸው የሊጉን ዋንጫ ያነሱት ካርሎ አንቼሎቲ፣ ከምርጥ የፕሪሚየር ሊግ አሰልጣኞች መካከል 10ኛ ደረጃን ይዘዋል።
ጣሊያናዊው አሰልጣኝ ቼልሲን በ2009/10 የውድድር ዘመን ፕሪሚየር ሊግን እና የኤፍ ኤ ዋንጫን በማሸነፍ ድርብ ድል አስመዝግበዋል።
በፕሪሚየር ሊጉ የእርስዎ የምንጊዜም ምርጥ አሰልጣኝ ማነው? ሀሳባችሁን አጋሩን።
በአዲስ የሺዋስ
@Ethiopian Broadcasting Corporation EBC-መዝናኛ #PremierLeague #football #sports #ebcdotstream
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: