ኢትዮጵያ በውጭ ወራሪዎች፣ በውስጥ ባንዳዎችና በጎረቤቶቿ የተቀናጀ ጫናና ወረራ ብትፈተንም፣ በጀግኖች ልጆቿ መሪነትና በፀና ህዝባዊ ደጋፊነቷ ሉዓላዊነቷን ያስከበረች ታላቅ ሀገር ናት።
ታሪካችንን ወደኋላ መለስ ብለን ስንቃኝ፣ ሀገራችን እንኳን ዛሬ ጥንትም የማትደፈርና ዳር ድንበሯን የምታስከብር ለመሆኗ የራስ አሉላ አባ ነጋ ታሪካዊ ተጋድሎ ትልቅ ማረጋገጫ ነው።
የኢጣሊያ ጦር ምድራችንን ለመውረር በቋመጠ ጊዜ ራስ አሉላ “እኔ የሮማ ጠቅላይ ገዥ ሆኜ ስሄድ ብቻ ነው ጣሊያኖች ሰሐጢ ድረስ ሊመጡ የሚችሉት፤ አንዴ ክንዴን አሳይቻቸዋለሁ፣ እንደገና ከመጡም እደግማቸዋለሁ፤ ራሱ ቀይ ባህር የኢትዮጵያ የተፈጥሮ ወሰን ሆኖ ኖሯል፣ ይኖራልም” ሲሉ የተናገሩት የቁርጠኝነት ቃል የዚሁ የታሪክ እውነት መገለጫ ነው።
ከቱርክ እስከ ኢጣሊያ በተጠነሰሰው ሴራ የኦቶማን ቱርኮች ምፅዋን በያዙ ጊዜ አፄ ዮሐንስ 4ኛ “እስክመጣ ጠብቁ” ቢሏቸውም፣ ራስ አሉላ “ለጌታ ድግስ እንጂ ጦር አላቆይም” በማለት የቱርክን ጦር ድባቅ መትተዋል።
ከሶስት ዓመታት በኋላ በድጋሚ የመጣውን የኢጣሊያ ጦር ድል ያደረጉ ሲሆን፣ በሽንፈቱ የተበሳጨው የኢጣሊያ መንግስት ለሁለተኛ ጊዜ ሶስት ክፍል ጦር አዘጋጅቶ ጥር 18 ቀን 1879 ዓ.ም በዶጋሊ ከራስ አሉላ ጋር ተፋጠጠ።
በዚሁ የዶጋሊ ጦርነት በቶማስ ዲ ክሪስቶፎሪስ ይመራ የነበረው የኢጣሊያ ጦር በራስ አሉላ ተፈጥሯዊ ወታደራዊ ስልትና በኢትዮጵያውያን ወኔ ድባቅ ተመቶ ከ500 በላይ ወታደሮቹ ተደምስሰዋል።
ይህ ድል በሮም ከፍተኛ ድንጋጤን የፈጠረ ሲሆን፣ እንግሊዝ የህይወት (Hewett) ውልን አፍርሳ ምፅዋን ለኢጣሊያ አሳልፋ ብትሰጥም፣ ራስ አሉላ በኩፊትና በዶጋሊ ባስመዘገቡት ድል ሀገራዊ ሉዓላዊነታችንን አስከብረዋል።
ከዶጋሊው ድል በኋላ ኢጣሊያ በጦርነቱ ለተደመሰሱት ወታደሮቿ በሮም “የአምስቱ መቶዎች አደባባይ” ሐውልት ስታቆም፣ ራስ አሉላ አባ ነጋ ግን በዓለም ህዝብ ልብ ውስጥ ዘላቂ የጀግንነት ሐውልታቸውን ተክለዋል።
የዶጋሊ ድል ኢትዮጵያ የፀረ-ቅኝ ግዛት ተጋድሎ ምልክት እንድትሆን ያደረገ እና ለታላቁ የዓድዋ ድል መነሻ የሆነ የመጀመሪያው ወሳኝ ምዕራፍ ነው።
“አሉላ አባ ነጋ የደጋ ላይ ኮሶ፣
በጥላው ያደክማል እንኳንስ ተቀምሶ”
እየተባለ የተገጠመላቸውና በጉንደት፣ በጉርዓ፣ በሰሐጢ፣ በመተማና በዓድዋ ሀገራቸውን ያስከበሩት ታላቁ አፍሪካዊ ጄነራል ራስ አሉላ አባ ነጋ የካቲት 8 ቀን 1889 ዓ.ም ቢያርፉም እኛ የነዚህ ታላላቅ የድል አባቶች ልጆች በመሆናችን በትናንቱ ታሪካችን እየኮራን ዛሬ የሚገባንን ስንጠይቅ በዘመኑ ቋንቋ የዲፕሎማሲ መርህን ተከትለን ነው።
በመሐመድ ፊጣሞ
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: