የሰላም ሚኒስትር አቶ መሐመድ እድሪስ ለዘመናት የቆዩ መሠረታዊ ሀገራዊ ችግሮችን በሠለጠነ መንገድ በውይይት እና በምክክር ለመፍታት የተጀመረው ታሪካዊው የሀገራዊ ምክክር ጉባኤ በስኬት መጠናቀቁን በማስመልከት ለመላው ኢትዮጵያውያን የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል።
ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው፣ ይህ ታሪካዊ ሂደት በሰላም፣ በታማኝነት፣ በታላቅ የኃላፊነት ስሜት እና በኢትዮጵያዊ ጨዋነት መጠናቀቁን አድንቀዋል።
"ሀገርን ለማሻገር በብልሃት መክሮ፣ ትውልድን አስተሣሥሮ ሌላ ዓድዋ ሠርቶ ማለፍ መታደል ነው፤ ተከብሮ የመኖርን መሠረትም ያጸናል" ሲሉ ገልጸውታል።
ሀገራችን የመከረችበት ይህ ጉባኤ የሕዝብን አሸናፊነት፣ የኢትዮጵያን ታላቅነት፣ የራስን ችግር በራስ የመፍታት ጥበብን እና የዓላማ አንድነትን በገሃድ ለዓለም ዳግም ያሳየ መሆኑንም አቶ መሐመድ እድሪስ አብራርተዋል።
ይህም አዲስ የሽግግር ተስፋ ምዕራፍን የሚያመላክት ደማቅ ድል መሆኑን ነው የጠቆሙት።
በምክክሩ የተገኙ የጋራ መግባባቶችን እና የሰላም ፍሬዎችን መንከባከብ እና መጠበቅ የሁሉም ዜጋ የጋራ ኃላፊነት በመሆኑ፣ መላው ኢትዮጵያውያን ተባብረው የነገዋን ጠንካራ፣ የበለጸገች እና ሁለንተናዊ ሰላሟ የተጠበቀ ኢትዮጵያን መሠረት እንዲያጸኑ ሚኒስትሩ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል።
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: