ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ተገኝተው ባደረጉት ንግግር ከጉባ ብስራቶች እና ሀገራዊ የማንሰራራት ፕሮጀክቶች መካከል አንዱና ዋነኛው የቤት ልማት ጉዳይ መሆኑን ገልጸው ነበር።
በባለፉት ሰባት ዓመታት 1.2 ሚሊዮን ቤቶች መገንባታቸውን በወቅቱ ያሳወቁት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ አሁን ደግሞ በሚቀጥሉት አምስት ዓመታት በመንግሥት፣ በግል እንዲሁም በመንግሥትና የግል አጋርነት ቢያንስ 1.5 ሚሊዮን ቤቶችን ለመገንባት መታቀዱን ይፋ አድርገዋል።
ይህንን ግብ ለማሳካት የ3D ቴክኖሎጂዎችን ጨምሮ ዘመናዊ አሠራሮችን ማስገባት፣ የኮንስትራክሽን ግብዓት ፋብሪካዎችን ማጠናቀቅ እና የሞርጌጅ ሥርዓት በመዘርጋት ዜጎች በረጅም ጊዜ ክፍያ የቤት ባለቤት የሚሆኑበት ወይም በተመጣጣኝ ዋጋ የሚከራዩበት መፍትሔ እንደሚበጀው ተናግረው ነበር።
ይህ በምክር ቤት የተገባው ቃል ሳይዘገይ በፍጥነት ወደ ተጨባጭ ተግባር መለወጡን የሚያሳይ ታሪካዊ እርምጃ ዛሬ ተወስዷል።
በኢትዮጵያ የመጀመሪያውን የተለየ የቤት መግዣ ብድር መልሶ ማጠናከሪያ ኩባንያ ለማቋቋም የሚያስችለውን ታሪካዊ የትብብር ማዕቀፍ ስምምነት በኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ እና በዓለም አቀፍ የፋይናንስ ኮርፖሬሽን (IFC) መካከል ተፈረሟል።
በ100 ቢሊዮን ብር ካፒታል የተቋቋመውና በIFC በኩል እስከ 200 ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ አስተዋፅኦ የሚደረግበት ይህ ታላቅ ተቋም፣ በባንክ ዘርፉ የሚታየውን የጥሬ ገንዘብ ፍሰት አለመመጣጠን በመቅረፍ ተደራሽ የቤት መግዣ ብድር እንዲኖር ያስችላል።
ይህም የተመጣጣኙን 1.5 ሚሊዮን ቤቶች ግንባታ ግብ የሚያሳካ፣ የግል ዘርፉን ተሳትፎ የሚያሳድግ እና ኢትዮጵያ ሁሉንም ያካተተ ኢኮኖሚ ለመገንባት የምታደርገውን ስኬታማ ጉዞ የሚያፋጥን ትልቅ የፖሊሲ እና የተግባር ውጤት ነው።
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: