Search

የ1954ቱ የአፍሪካ ዋንጫ ድል ትውስታ እና አሁን የተሰነቀው ተስፋ

ሓሙስ ነሐሴ 28, 2018 102

የኢትዮጵያ እግር ኳስ በአፍሪካ መድረክ የነገሠበት፣ ሰንደቅ ዓላማዋ በአኅጉሪቱ ትልቁ የስፖርት መድረክ ላይ ከፍ ብሎ የተውለበለበበት ብሎም ኢትዮጵያ ለአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ የምታልም ሳትሆን የዋንጫው ባለቤት የነበረችበት ወርቃማ የታሪክ ምዕራፍ ነበር።

ጥር 13 ቀን 1954 . አዲስ አበባ የአፍሪካ እግር ኳስ መናኸሪያ ሆና 3ኛውን የአፍሪካ ዋንጫ ስታስተናግድ፣ አስተናጋጇ ኢትዮጵያ ለፍጻሜው ደረሰች። በኢትዮጵያ እና በታሪካዊው ድል መካከል የቆመው ደግሞ የወቅቱ ሻምፒዮን የነበረው የግብጽ ብሔራዊ ቡድን ነበር።

በቀዳማዊ አጼ ኃይለሥላሴ ስታዲየም (የአሁኑ አዲስ አበባ ስታዲየም) የተሰበሰቡ በሺዎች የሚቆጠሩ ደጋፊዎች በኢትዮጵያ ስፖርት ታሪክ ውስጥ ትልቁን ድንቅ ምዕራፍ ለመመልከት ታደሙ። ፍልሚያው ግን እጅግ ፈታኝ ነበር።

35ኛው ደቂቃ ባዳዊ አብደል ፈታሕ ግብ አስቆጥሮ ግብጾችን መሪ አደረገ። በሁለተኛው አጋማሽ ግርማ ተክሌ አቻ ቢያደርግም፣ ባዳዊ 75ኛው ደቂቃ ሁለተኛ ግቡን በማስቆጠር ኢትዮጵያን ከሽንፈት አፋፍ ላይ አድርሷት ነበር። ሆኖም 84ኛው ደቂቃ ላይ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፈርጥ መንግሥቱ ወርቁ ባስቆጠራት አስደናቂ ግብ መደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ 2 2 ተጠናቅቆ ወደ ጭማሪ 30 ደቂቃ አመራ።

በጭማሪው ሰዓት የታሪክ ገጾች ለኢትዮጵያ በደማቁ ተጻፉ። 101ኛው ደቂቃ ኢታሎ ቫሳሎ ኢትዮጵያን መሪ ሲያደርግ፣ ጨዋታው ሊጠናቀቅ ጥቂት ደቂቃዎች ሲቀሩት መንግሥቱ ወርቁ ለራሱ ሁለተኛዋን ግብ በማስቆጠር ውጤቱን 4 2 አደረገው። የዳኛው የመጨረሻ ፊሽካ ሲሰማ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ሻምፒዮን መሆኗ ታወጀ።

በዕለቱ በአዲስ አበባ ጎዳናዎች ላይ የነበረው ደስታ እና ሕዝቡ በሬዲዮ ዙሪያ ተሰብስቦ እያንዳንዱን እንቅስቃሴ ይከታተልበት የነበረው ስሜት ወደር አልነበረውም።

ንጉሠ ነገሥቱ ቀዳማዊ አጼ ኃይለሥላሴ ዋንጫውን ለአንበሉ ሉቺያኖ ቫሳሎ ሲያስረክቡ የታየው ምሥል የሀገር ብሔራዊ ኩራት መገለጫ ሆኖ ለትውልድ ተላልፏል።

ኢትዮጵያ በመጀመሪያው 1949 የአፍሪካ ዋንጫ ሁለተኛ፣ 1951 ሦስተኛ ደረጃን ይዛ ካጠናቀቀች በኋላ ነው 1954 በግማሽ ፍጻሜው ቱኒዚያን 4 2 እንዲሁም በፍጻሜው ግብጽን በተመሳሳይ 4 2 በማሸነፍ በሁለት ጨዋታዎች 8 ግቦችን አስቆጥራ ታሪካዊውን ዋንጫ ወደ ቤቷ ያስገባችው።

ድል ለሀገራቸን 64 ዓመታት በኋላ ዛሬም ድረስ ብቸኛው የአፍሪካ ዋንጫ ሆኖ ይገኛል። የእግር ኳስ ዓለም ተቀይሯል፤ ውድድሩም በገንዘብ፣ በስታዲየሞች ደረጃ እና በታክቲክ እጅግ የበለጸገ ሆኗል።

ነገር ግን የመንግሥቱ ወርቁ፣ የሉቺያኖ ቫሳሎ፣ የኢታሎ ቫሳሎ እና የግርማ ተክሌ አሻራ በታሪክ መዝገብ ውስጥ ሕያው ሆኖ ይኖራል።

ዛሬ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ዋንጫን ዳግም ለማስተናገድ እና ወደ አኅጉሩ የውድድር መድረክ በድምቀት ለመመለስ በምታልምበት ወቅት፣ ይህንን ታሪካዊ ድል ማስታወስ ለወደፊቱ ጉዞ ትልቅ ብርታት ነው።

ምክንያቱም የኢትዮጵያ እግር ኳስ ከዚህ ቀደም በአፍሪካ ማማ ላይ ነበር፤ ሀገራችን ዋንጫውንም አሸንፋለች።

በመሆኑም ወደፊት የአፍሪካ መድረክ ላይ ስኬታማ ለመሆን የሚደረገው ጥረት የነገ ሕልም ብቻ ሳይሆን፣ ትናንት በተግባር የተረጋገጠ የታሪክ እውነት ጭምር ነው።

በእሱባለው ተሾመ

 

አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: