ኢትዮጵያን ጨምሮ 181 አባል ሀገራት የተሳተፉበት የዓለም አቀፉ የአቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲ (IAEA) 70ኛ አጠቃላይ ጉባኤ በኦስትሪያ ቪየና በይፋ መካሄድ ጀምሯል።
በጉባኤው መክፈቻ ላይ የኤጀንሲው ዋና ዳይሬክተር ሚስተር ራፋኤል ግሮሲ ባለፈው ዓመት የተከናወኑ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ሥራዎችን እንዲሁም ያመጧቸውን በጎ ተጽዕኖዎች አብራርተዋል።
በጉባኤው ላይ የየሀገራቱ ተወካዮች ከኒውክሊየር ደህንነት፣ ጥበቃ እና ቴክኖሎጂ ትግበራ ጋር የተያያዙ እንቅስቃሴዎችን ለማጠናከር በጥልቀት እንደሚመክሩ ተነግሯል።
በተጨማሪም ኤጀንሲው የ2025 ዓመታዊ ሪፖርቱን፣ የ2027 የበጀት ማሻሻያን እና የፋይናንስ ሪፖርቶችን ገምግሞ የአስተዳደር ቦርድ አባላትን እንደሚመርጥ ተገልጿል።
በዚህ ዓለም አቀፍ ጉባኤ ላይ በጄኔቫ የኢትዮጵያ ቋሚ መልክተኛ ጽሕፈት ቤት ምክትል ሚሲዮን መሪ አምባሳደር ኃይለሥላሴ ሱባ እንዲሁም ሁለተኛ ጸሐፊ ወ/ሮ ቤተልሔም መኮንን የኢትዮጵያን ልዑክ በመምራት ተሳትፎ እያደረጉ እንደሚገኙ የኢትዮጵያ ኒውክሊየር ኃይል ኮሚሽን መረጃ አመልክቷል።
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: