Search

የኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለ ንዋዮች ገበያ፦ የፋይናንስ ዘርፍ አዲስ የንጋት ጮራ

ቅዳሜ መስከረም 09, 2019 52

በኢትዮጵያ የፋይናንስ ታሪክ ትልቅ የለውጥ ምዕራፍ የከፈተው የኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለ ንዋዮች ገበያ፣ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴን ወደ ዘመናዊ የካፒታል ሥርዓት የሚያሸጋግር ዋና ምሰሶ ሆኖ ብቅ ብሏል።

ይህ ገበያ የንግድ ድርጅቶችም ሆኑ ዐበይት የመንግሥት ፕሮጀክቶች በባንክ ብድር ላይ ብቻ ጥገኛ የሚሆኑበትን የቆየ አሠራር በመቀየር ሰፊ እና ዘመናዊ የፋይናንስ አማራጭ እያቀረበ ይገኛል።

ተቋሙ በመንግሥት እና በግሉ ዘርፍ አጋርነት የተቋቋመ ሲሆን፣ በባለቤትነት መዋቅሩም 25 በመቶው በመንግሥት የልማት ድርጅቶች እና በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ እንዲሁም ቀሪው 75 በመቶ ደግሞ በሀገር በቀል የግል ንግድ ባንኮች፣ በኢንሹራንስ ኩባንያዎች እና በውጭ ስትራቴጂያዊ ባለሀብቶች የተያዘ ነው።

ይህ የተመጣጠነ መዋቅር ገበያው በገለልተኝነት፣ በግልጽነት እና በተጠያቂነት እንዲመራ ጠንካራ መሠረት ጥሏል። የኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለ ንዋዮች ገበያ የአክሲዮን፣ የቋሚ ገቢ ሰነዶች እና 'ኢንተርባንክ' የገንዘብ ገበያ ዘርፎችን አቅፎ በመያዝ ወደ ተግባር ገብቷል።

የገበያውን ታማኝነት እና ደኅንነት ከማረጋገጥ አኳያም የኢትዮጵያ የካፒታል ገበያ ባለሥልጣን ጠንካራ የቁጥጥር ሥርዓት በመዘርጋት የኢንቨስተሮችን መብት በማስጠበቅ ላይ ይገኛል።

ገበያው ወደ ሥራ ከገባበት ጊዜ ጀምሮ አበረታች እና ተጨባጭ ውጤቶችን እያስመዘገበ ነው። ለዚህም ትልቁ ማሳያ ኢትዮ ቴሌኮም በግንቦት ወር 2018 . በይፋ በዋናው ገበያ ላይ ተመዝግቦ ወደ ግብይት መግባቱ ነው።

የኢትዮ ቴሌኮም አክሲዮኖች ወደ ገበያ ከገቡበት ጊዜ ጀምሮ ከፍተኛ የዋጋ ጭማሪ በማሳየት በባለሀብቶች ዘንድ ልዩ መነቃቃትን ፈጥረዋል።

ከዚህ ጎን ለጎንም ግንባር ቀደም የፋይናንስ ተቋማት የሆኑት አዋሽ፣ ዓባይ፣ አቢሲኒያ፣ ገዳ እና ወጋገን ባንኮች በገበያው ተመዝግበው እና አክሲዮን ገዝተው በንቃት እየተሳተፉ ይገኛሉ።

ሌላው ትልቁ ስኬት በባንኮች መካከል ያለውን የገንዘብ ፍሰት ለማሳለጥ የተዘረጋው 'ኢንተርባንክ' ገበያ ነው። ይህ የግብይት ሥርዓት ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ እስከ መስከረም 2018 . ድረስ ባለው አጭር ጊዜ ውስጥ 3 ትሪሊዮን ብር በላይ የግብይት መጠን በማስተናገድ ከፍተኛ ዕድገት አሳይቷል።

በሌላ በኩል ዜጎች በዲጂታል መንገድ በቀላሉ በካፒታል ገበያው መሳተፍ እንዲችሉ "ንዋይ" የተሰኘ መተግበሪያ በሥራ ላይ አውሏል።

እነዚህ የዲጂታል አማራጮች ኢንቨስተሮች በቀጥታ የገበያውን መረጃ እንዲከታተሉ፣ ከአሻሻጮች ጋር እንዲገናኙ እና ግብይቶችን ያለምንም እንግልት እንዲፈጽሙ ሰፊ ዕድል ከፍተዋል።

ከዓለም አቀፍ እና ቀጣናዊ ተሞክሮዎች አንጻር የጎረቤት ኬንያ የናይሮቢ ሰነደ ሙዓለ ንዋዮች ገበያ ትላልቅ ተቋማትን ወደ ግል በማዛወር እና የመሠረተ ልማት ቦንዶችን በማውጣት ለኢኮኖሚ ዕድገት የላቀ ሚና ተጫውቷል።

የኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለ ንዋዮች ገበያም ይህንን ተሞክሮ በመቀመር ኢትዮጵያ በትራንስፖርት፣ በኃይል እና በሌሎች ቁልፍ ዘርፎች የሚያስፈልጋትን ከፍተኛ የመሠረተ ልማት በጀት ከራሷ የካፒታል አቅም እንድታሟላ ያግዛታል።

በመንግሥት በኩልም በጀት ለመሸፈን በቀጥታ ከብሔራዊ ባንክ ገንዘብ ከመበደር ይልቅ በሰነደ ሙዓለ ንዋይ ገበያ በኩል 'ትሬዠሪ' ቢል እና 'ቦንድ' በመሸጥ ፋይናንስ ማግኘቱ የዋጋ ንረትን ለመቆጣጠር ትልቅ አቅም ይፈጥራል።

አነስተኛ እና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞችም የመያዣ ንብረት ሳይጠየቁ በካፒታል ገበያው በኩል ፋይናንስ የሚያገኙበት ዕድል በመፈጠሩ የሥራ ፈጠራን እና አጠቃላይ የኢኮኖሚ ዕድገትን ወደ አዲስ ምዕራፍ እንደሚያሸጋግረው ታላቅ ተስፋ ተጥሎበታል።

በለሚ ታደሰ

 

አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: