ወጋገን ባንክ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከታክስ በፊት 4.3 ቢሊዮን ብር ትርፍ እና ከታክስ በኋላ 3.1 ቢሊዮን ብር የተጣራ ትርፍ ማስመዝገቡን ይፋ አድርጓል።
የወጋገን ባንክ አ.ማ የባለአክሲዮኖች 33ኛ መደበኛ እና 16ኛ አስቸኳይ ጠቅላላ ጉባኤ በሂልተን ሆቴል በመካሄድ ላይ ይገኛል።
የባንኩ የዳይሬክተሮች ቦርድ ዋና ሰብሳቢ አቶ አብዲሹ ሁሴን እንዳስታወቁት፣ ባንኩ በበጀት ዓመቱ 16.4 ቢሊዮን ብር አጠቃላይ ገቢ ያገኘ ሲሆን፣ ይህም ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር የ21 በመቶ ዕድገት አሳይቷል።
የባንኩ የተከፈለ ካፒታል የ44 በመቶ ዕድገት በማሳየት 10.1 ቢሊዮን ብር መድረስ የቻለ ሲሆን፣ አጠቃላይ ሀብቱም 111.3 ቢሊዮን ብር መድረሱ ተገልጿል። በተመሳሳይ ከደንበኞች የተሰበሰበው የተቀማጭ ገንዘብ መጠን በ23 በመቶ በማደግ 81.6 ቢሊዮን ብር መድረሱን ባንኩ አስታውቋል።
ለተለያዩ የኢኮኖሚ ዘርፎች የሰጠው አጠቃላይ የብድር መጠንም 67.3 ቢሊዮን ብር መድረሱ በጉባዔው ላይ ተጠቅሷል።
በተጨማሪም ባንኩ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 366 ሚሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሬ ማግኘት የቻለ ሲሆን፣ ይህም ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ34 በመቶ ጭማሪ ማሳየቱን አቶ አብዲሹ ጠቅሰዋል።
የዳይሬክተሮች ቦርድ ዋና ሰብሳቢው አክለውም፣ ባንኩ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በርካታ ፈተናዎችን በማለፍ ስኬታማ ጊዜን ማሳለፉን ገልጸው፣ ቀጣይነት ያለው ዕድገት እያስመዘገበ እንደሚገኝም አብራርተዋል።
በአባዲ ወይናይ
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: