ገዳ ባንክ 5ኛውን የባለአክሲዮኖች ጠቅላላ ጉባዔ በዛሬው ዕለት በአዲስ ዓለም አቀፍ የኮንቬንሽን ማዕከል አካሂዷል።
በጉባዔውም የባንኩ የዳይሬክተሮች ቦርድ ዓመታዊ የኦዲት ሪፖርት ያቀረበ ሲሆን፣ በባንኩ ዓመታዊ የትርፍ መጠን እና ቀጣይ አቅጣጫዎች ላይ ሰፊ ውይይት ተደርጓል።
የገዳ ባንክ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ወልዴ ቡልቶ በጉባዔው ላይ እንዳብራሩት፣ ባንኩ ወደ ሥራ ከገባ ሦስት ዓመት ብቻ ቢሆነውም የኢትዮጵያን የፋይናንስ ፖሊሲ በአግባቡ ተከትሎ በመሥራቱ የ64 በመቶ ዕድገት ማስመዝገብ ችሏል። በዚህም የባንኩ አጠቃላይ ካፒታል ከ16 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር በላይ መድረሱን ዋና ሥራ አስፈጻሚው አስታውቀዋል።
በተጠናቀቀው በጀት ዓመትም ባንኩ ከ2 ቢሊዮን ብር በላይ ትርፍ ማግኘት መቻሉም በጉባዔው ላይ ይፋ ተደርጓል።
የባንኩን ተደራሽነት ከማስፋት አኳያ መላውን የኢትዮጵያን ክፍሎች ባሳተፈ መልኩ የአክሲዮን ሽያጭ እየተከናወነ መሆኑ እና የባለአክሲዮኖች ቁጥርም ከ28 ሺህ ወደ 32 ሺህ ከፍ ማለቱ ተገልጿል።
በአሁኑ ወቅትም ከተዘጋጀው የባንኩ አክሲዮን ውስጥ ከ60 በመቶ በላይ መሸጡን ነው አቶ ወልዴ የተናገሩት።
በመሠረተ ልማት ግንባታ ረገድም፣ ገዳ ባንክ ዘመናዊ የዋና መሥሪያ ቤት ሕንፃ ለመገንባት ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቦታ ተረክቦ የግንባታ ሂደቱን እያከናወነ እንደሚገኝ በጉባዔው ላይ ተመላክቷል።
በዓሊ ደደፎ
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: