ሉሲ እና ሰላም በማዕከላዊ አውሮፓ ቼክ ሪፐብሊክ ፕራግ ከተማ በዛሬው ዕለት መጎብኘት ጀምሯል።
የዚህ ኤግዚብሽን ይፋዊ መክፈቻ የቼክ ጠቅላይ ሚኒስትር ፒተር ፊያላ እና የቱሪዝም ሚኒስትር ሰላማዊት ካሳ በተገኙበት ተካሂዷል።
የቱሪዝም ሚኒስትር ሰላማዊት ካሳ በኤግዚቢሽኑ ላይ ባደረጉት ንግግር፤ የሉሲና ሰላም ቅሪተ አካሎች በቼክ መገኘት በተለይ ለታሪክ አጥኚዎች ዋጋ የማይተመንለት ዕድል ነው ብለዋል።
ሉሲና ሰላም መጪዋን አዲሷን ኢትዮጵያም ለማስተዋወቅ እድል ይሰጣል ሲሉ ተናግረዋል።
ሚኒስትሯ ኢትዮጵያን መጥታችሁ ጎብኙ ሲሉም ጥሪ አቅርበዋል።
የቼክ ሪፐብሊክ ጠቅላይ ሚኒስትር ፒተር ፊያላ፥ የሰው ልጅ አመጣጥን የሚያሳየውን ኤግዚቢሽን ለማካሄድ በብዙ ተዘጋጅተናል ሲሉ ገልፀዋል።
ሉሲና ሰላም ጋር በአካል መጥታችሁ የት ነን ?ከየት መጣን? የሚለውን ለልጆቻችሁ አሳዩ ሲሉም ጠቅላይ ሚኒስትሩ መልዕክት አስተላልፈዋል።
የቼክ ብሔራዊ ሙዚየም ዳይሬክተር ሚካኤል ሉካሽ (ዶ/ር)፥ ይህ ኤግዚቢሽን ለሁለቱ ሀገራት ትስስር ትልቅ አስተዋፆ አለው ያሉ ሲሆን ኢትዮጵያም ይህን እንቁ ዕድል ስለሰጠችን እናመሰግናለን ብለዋል።
በቼክ ሪፐብሊክ ብሔራዊ ሙዚየም እየተካሄደ የሚገኘው ኤግዚቢሽን ለ60 ቀናት ይቆያል።
በመቅደላዊት ደረጀ