Search

ኢትዮጵያን በጠንካራ መሠረት ላይ ለማፅናት በተጀመረው ተግባራዊ ሥራ የግል ተቋማት ሚና ከፍተኛ ነው - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ

ቅዳሜ ጳጉሜን 01, 2017 37

ኢትዮጵያን በጠንካራ መሠረት ላይ ለማፅናት በጀመርነው ተግባራዊ ሥራ ሀገራዊ ተቋሞቻችን ከፍተኛ ሚና አላቸው ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ።

በመሆኑም የሀገራችንን የዕድገት ጉዞ ለማስቀጠል እና ስኬታማ ለማድረግ እንደ ሚድሮክ ያሉ ተቋማት አበርክቷቸው የላቀ ነው ብለዋል።

የፅናት ቀን ብለን በሰየምነውዛሬው ዕለት የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ በተሰማራባቸው ዘርፎች የሚያመርታቸውን ምርቶች እና አገልግሎቶች የሚያስቃኝ አውደርዕይ ተመልክተናል ብለዋል።

ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ለኢትዮጵያ በተለያዩ ፈታኝ ወቅቶች ጭምር በፅናት በመሥራት ሕዝባዊነታቸውን ካረጋገጡ እና ለሀገር ኢኮኖሚያዊ እንዲሁም ማኅበራዊ ልማት ከፍተኛ ሚና ከተጫወቱት ተቋማት መካከል ግንባር ቀደሙ ነው ሲሉ አክለዋል።

ጠንካራ ኢኮኖሚ ለመገንባት በምናደርገው ጉዞ ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ከግብርና እስከ ማኑፋክቸሪንግ፣ ከሆቴልና ቱሪዝም እስከ ማዕድን በተለያዩ ዘርፎች በስፋት በመሰማራት እያበረከተው ያለው አስተዋጽኦ ከፍተኛ እንደሆነ መመልከት ችለናል ብለዋል

በደም እናአጥንት የፀናችው ኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ልዕልናዋ እንዲረጋገጥ የግሉ ዘርፍ በሀገራዊ ልማት የሚያበረክተው አስተዋፅኦ ከፍ ያለ ድርሻ ይይዛል ነው ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው።

መንግሥት ለግሉ ዘርፍ የሰጠው ትኩረት እና የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ፖሊሲ ማሻሻያ ማዕቀፉ እንደ ሀገር የፀና ኢኮኖሚ ለመገንባት የሚደረገውን ጥረት የሚያፋጥን ሆኖ ፍሬውን መመልከት እንደተጀመረም ጠቁመዋል።

ሚድሮክ ባሉት 45 ኩባንያዎች ለሀገር እና ሕዝብ ከሚያበረክተው ቀጥተኛ ድጋፍ ባለፈ ምርቶቹን በቅናሽ ዋጋ ለኅብረተሰቡ ማቅረቡ፣ ሌሎች ተቋማት የገበያ ትሥሥር እንዲፈጠርላቸው በር መክፈቱ እና የካበተ ልምዱን ለማሳወቅ የዛሬውን አውደርዕይ ማዘጋጀቱ በአርአያነት የሚጠቀስ ተግባር ነው ብለዋል።

የሀገር ዕድገት እና ብልፅግናን እውን ለማድረግ ከግሉ ዘርፍ ተሳትፎ ውጪ የሚታሰብ አይደለም ነው ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፤ ዘመናትን የተሻገረ ልምድ ያላቸው ሚድሮክን መሰል ተቋማት ተሞክሯቸውንማጋራት እና ሕዝባዊነታቸውን በማረጋገጥ ኢትዮጵያን ማፅናት እንደሚጠበቅባቸው አሳስበዋል።

#EBCdotstream #midroc #resilience