የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ ልዑክ በተባበሩት ዐረብ ኤምሬቶች ከሚገኙ የተለያዩ የማኅበረሰብ አባላት ጋር ዛሬ የአጀንዳ ማሰባሰቢያ መድረክ በዱባይ ከተማ እያካሄደ ይገኛል፡፡
መርሃ ግብሩ በሐይማኖት አባቶች ፀሎት ተጀምሯል፡፡

በመድረኩ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የኮሚሽኑ ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርዓያ በተባበሩት ዐረብ ኤምሬቶች የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ለሀገራዊ የልማት ፕሮጀክቶች ከፍተኛ ድጋፍ በማድረግ ለሀገራቸው ያላቸውን ፍቅር በተግባር ያሳዩ መሆናቸውን አስታውሰዋል።
አሁን ደግሞ ለኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላም ቁልፍ በሆነው በሀገራዊ ምክክር ላይ ንቁ ተሳትፎ በማድረግ እና አጀንዳዎቻቸውን በነፃነት በማቅረብ በምክክሩ ሒደት የሚኖራቸውን ሚናቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ ጥሪ አቅርበዋል፡፡

በመድረኩ ኮሚሽኑ እስካሁን ስላከናወናቸው ተግባራት ገለጻ የተሰጠ ሲሆን፤ ተሳታፊዎቹም በቡድን ተከፋፍለው በመወያየት አጀንዳዎቻቸውን በማጠናቀር ላይ መሆናቸውን ከኮሚሽኑ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።