የልብ ፍቅር ምን እንደሆነ ለሚያውቀው እና ፍቅርን በተግባር እየኖረ ላለው ለከሚሴ እና ለወሎ ሕዝብ መንገር አይጠበቅብንም ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ተናገሩ፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዛሬ በከሚሴ ተገኝተው ባደረጉት ንግግር፤ የወሎን የመሰለ የልብ ፍቅር ካለ ክፋት እና ጥላቻ መቼም እንደማያሸንፉ ገልጸዋል፡፡
የወሎ ሕዝብ ፍቅር እንኳን ለወሎ ለመላው ኢትዮጵያም የሚተርፍ መሆኑን ነው የጠቀሱት፡፡
የከሚሴ እና የወሎ ሕዝብ እንደሚያውቀው ሰላም ከእውነተኛ ልብ ይመነጫል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ የወሎ ሕዝብ ደግሞ በዚህ በኩል ለሌላውም የሚተርፍ ፍቅር እንዳለው ተናግረዋል፡፡
የከሚሴ ሕዝብ በጀግንነት፣ በፍቅር እና በጠንካራ ሠራተኛነቱ ይታወቃል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ፤ ይህን ማንነቱን ደግሞ ከልጅነታቸው ጀምረው ሲሰሙት እንደነበር ጠቅሰዋል፡፡
"ከብዙ ዓመታት ናፍቆት በኋላ በጣም ከምንወደው ሕዝብ ጋር እንደዚህ በዓይነ ሥጋ በመገናኘቴ በጣም ደስተኛ ሆኛለሁ፤ ፈጣሪንም አመሰግናለሁ" ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፡፡
የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ ይህን ፍቅር መገለጫው የሆነውን ሕዝብ እንዳገኝ ስለመቻቹልኝ አመሰግናለሁ ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ሰላም እና የልብ መቀራረብ ካለ ሁሉም ነገር በጊዜው ይሆናል ብለዋል፡፡
በለሚ ታደሰ
#Ebc #Ebcdotstream #Ethiopia #AbiyAhmedAli #Kemise #Wollo