የኢትዮጵያ ብልጽግና እና ምልዑነት የሚጓደለው ኢትዮጵያውያን በኅብረት መትጋት እና መስራት ካልቻሉ ብቻ ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለጹ፡፡
20ኛው የኢትዮጵያ ብሔሮች ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ቀን "ዴሞክራሲያዊ መግባባት ለኅብረ ብሔራዊ አንድነት" በሚል መሪ ሀሳብ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ሆሳዕና ከተማ ተከብሯል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚሁ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት፤ ኢትዮጵያ በርከት ያሉ ችግሮች ያሉባት ቢሆንም በእጅጉ ልንጠቀምበት የሚገባ በርካታ አቅምም ያላት ሀገር ናት ብለዋል፡፡
ይህ ትውልድ የኢትዮጵያን ችግሯን ብቻ ሳይሆን አቅሟን ፈልፍሎ የማየትናየማውጣት ብቃት እንዳለው ከጅምር ስራችን የሚታይ ነው ብለዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ብዙ እጆች በትብብር ካልሰሩ እህል ዳቦ እንደማይሆን አስገንዝበው፤ በትብብር መንፈስ በብዙ ትጋት እና ልፋት አዲስ የታሪክ ገፅ መክፈት ይገባል ብለዋል።
በእኛም በሌሎችም የሚታመንበት፣ ለትምህርት የሚውል ዳግም ዓድዋ በኢትዮጵያ ይከበር ዘንድ፣ ዛሬ አፍሪካ የምትፈልገው ብልጽግና ነውና ይህንን ለማሳካት በጋራ እንቁም የሚል መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡
የተዋበች፣ የላቀች እና የጸናች ሀገር ለልጆቻችን ማስረከብ እንድንችል ዛሬ የተሰጠንን ዕድል እንጠቀም ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፡፡
በመሐመድ ፊጣሞ