የሀላላ ድንጋይ ካብ (ሀላላ ኬላ) የዳውሮ አባቶች በአገር በቀል ዕውቀት ድንጋይን በድንጋይ ላይ በማነባበር የገነቡት ግዙፍ እና ረዥም የድንጋይ ግንብ ነው።
የሀላላ ካብ በ1 ሺህ 532 ዓ.ም በዳውሮ የመጀመሪያ ንጉሥ ስራው ተጀምሮ እስከ 18ኛው ክፍለ ዘመን ዳውሮን ያስተዳድሩ በነበሩ 14 ነገሥታት በቅብብሎሽ የተገነባ እንደሆነ ይነገራል።
አጠቃላይ የግንባታ ሂደቱ 350 ዓመታት የወሰደ ሲሆን በንጉሥ ካዎ ሀላላ መጠሪያ "ሀላላ ኬላ" የሚል ስያሜን አግኝቷል።
"ሃላላ" የንጉሱ ስም ሲሆን “ኬላ” የሚለው ደግሞ የድንጋይ ካብ ማለት ነው።
የድንጋይ ካቡ አካባቢውን ከውጪ ወራሪ ኃይል ጦር ለመከላከል የተገነባ እንደሆነ የታሪክ ተመራማሪ ታዬ ጊምባቶ ገልጸዋል።
ሀላላ የድንጋይ ካብ በተለይም ዳውሮን ከውጪ ወራሪ ኃይል ፈረሰኛና እግረኛ ጦር ለመከላከል የተገነባ መሆኑን አቶ ታዬ አንስተዋል።
በሰባት ረድፍ አጠቃለይ ርዝመቱ 1 ሺህ 225 ኪ.ሜ የሚሸፍነው ሀላላ ኬላ፤ ከ2.5 እስከ 5 ሜትር ስፋትና ከ2.5 እስከ 3.8 ሜትር በላይ ከፍታ እንዳለው የታሪክ ተመራማሪው ገልጸዋል።
የድንጋይ ካቡ ከ500 በላይ ዕድሜ ቢኖረውም ምንም አይነት ጉዳት ሳይደርስበት ጥሩ ሁኔታ ላይ እንደሚገኝም አቶ ታዬ ተናግረዋል።
ሀላላ ካብ የዳውሮ ህዝብ አንድነት ማሳያ መሆኑን እንዲሁም ካቡ በሚሰራበት ጊዜ እዛው እየዋሉ እያደሩ ህብረተሰቡ ስንቅ በማቀበል ስራውን ጨርሰው እንደወጡ ይህም ለቀጣይ ትውልድ ጥሎት ያለፈው አሻራ ማሳያ መሆኑን አንስተዋል።
በቢታንያ ሲሳይ
#Ebc #Ebcdotstream #Ethiopia #Dawro #HalalaKella