ሎጎ ሐይቅ ሪዞርት የሀገርን ገጽታና የሕዝብን ክብር ከፍ የሚያደርጉ ፕሮጀክቶችን በአካባቢው ለመገንባት ምሳሌ ሆኖ የሚያገለግል የስበት ማዕከል ነው ሲሉ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ ገለጹ።
ደሴንና ኮምቦልቻን እንዲሁም በቅርብ ርቀት የሚገኙ ሳተላይት ከተሞችን በማገናኘት ወደፊት ለሚመሰረት ግዙፍ ከተማ ትልቅ አቅም ሆኖ የሚያገለግል ፕሮጀክት ነው ብለዋል።
እንዲህ ዓይነት ግዙፍ ፕሮጀክቶች በሚያስገርም ፍጥነትና ጥራት ሊጠናቀቁ የቻሉት በመልማት ላይ ያተኮሩ ዓይኖች፣ መበልፀግን የሚያሰላስል የልቦና ውቅርና በጎ የመሥራት ውጤት በመሆናቸው ነው ሲሉ አቶ አረጋ ተናግረዋል።
እንደ ባለሀብቱ አቶ በላይነህ ክንዴ ሁሉ ሌሎች ቀና ሐሳብ ያላቸው ባለሀብቶችም ወደ ክልሉ መጥተው እንዲሰማሩ፣ ራሳቸውንም ሆነ ወገናቸውን እንዲጠቅሙ ርዕሰ መስተዳድሩ ጥሪ አቅርበዋል።
የሎጎ ሐይቅ ሪዞርት ምርቃት ለክልሉ የቱሪዝም ዘርፍና ለከተሞች ዕድገት አዲስ ተስፋ ይዞ የመጣ መሆኑም ተመላክቷል።
በመሀመድ ፊጣሞ