በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጋሞ ዞን በተከሰተው ድንገተኛ የመሬት ናዳ አደጋ ጉዳት የደረሰባቸውን ወገኖች ለማጽናናት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ጥላሁን ከበደ እና የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ወ/ሮ አለምፀሀይ ጳውሎስ በአደጋው ስፍራ ተገኝተዋል።
በዞኑ ደጋማ ወረዳዎች የጣለውን ከፍተኛ ዝናብ ተከትሎ በተከሰተው በዚህ አደጋ በሰው ሕይወትና በንብረት ላይ ከፍተኛ ጉዳት የደረሰ ሲሆን፣ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎቹ በአደጋው ሕይወታቸውን ላጡ ወገኖች የተሰማቸውን ጥልቅ ሐዘን በመግለጽ ለቤተሰቦቻቸውና ለወዳጅ ዘመዶቻቸው መጽናናትን ተመኝተዋል።
ርዕሰ መስተዳድሩ አደጋው በደረሰበት ስፍራ ተገኝተው የጉዳቱን መጠን የተመለከቱ ሲሆን፣ መንግሥት ከተጎጂዎች ጎን በመቆም አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግም አረጋግጠዋል።
በጋሞ ዞን ጋጮ ባባ ወረዳ ማዞ ዶይሳ ቀበሌ በተከሰተው የመሬት ናዳ አደጋ እስካሁን ባለው መረጃ መሠረት የ52 ሰዎች ሕይወት ያለፈ ሲሆን፣ የጠፉ ወገኖችን አስክሬን የመፈለግና የማውጣት ሥራው ቀጥሏል።