ለዘመናት በዝምታ ታልፎ የቆየው የኢትዮጵያ የባሕር በር ጥያቄ በአሁኑ ወቅት በመደመር መንግሥት የኅልውና እና የብሔራዊ ጥቅም ዋነኛ አጀንዳ ሆኖ ቀርቧል። ይህም በኢትዮጵያ ጂኦ-ፖለቲካዊ ጉዞ ላይ ትልቅ የታሪክ ምዕራፍ ከፍቷል።
ጉዳዩ ከታሪካዊ ስህተትነት ወደ አንገብጋቢ የልማት እና የደኅንነት ጥያቄነትም ተሸጋግሯል። ኢትዮጵያ በ“መልክዓ ምድራዊ እስር ቤት” ውስጥ ለዘላለም መቆየት እንደማትችል እና የባሕር በር ማግኘት ከ130 ሚሊዮን በላይ ለሆነው ሕዝብ የፍትሕ ጥያቄ መሆኑን መንግስት በይፋ አስታውቋል።
ይህ ስልታዊ ፖሊሲ ከፕሮፌሰር ያዕቆብ ኃይለማርያም የሕግ እና የታሪክ ትንታኔዎች ጋር መመሳሰሉ፣ ለጥያቄው ሕጋዊ ዕውቅና ለማግኘት የሚደረገውን ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ይበልጥ ያጠናክረዋል።
ኢትዮጵያ በታሪካዊ፣ ሕጋዊ እና ጂኦ-ፖለቲካዊ ምክንያቶች ወደ ቀይ ባሕር የምታደርገው ጉዞ የኅልውና እና የትውልድ ጥያቄ መሆኑን ፕሮፌሰር ያዕቆብ ኃይለማርያም “አሰብ የማን ናት?” በሚለው መጽሐፋቸው በሰፊው ተንትነዋል።
የቀድሞው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ከፍተኛ የሕግ አማካሪ እና የዓለም አቀፍ ወንጀለኞች ችሎት ዓቃቤ ሕግ የነበሩት ፕሮፌሰር ያዕቆብ፣ በ2003 ዓ.ም ባሳተሙት በዚሁ መጽሐፍ የኢትዮጵያ የባሕር በር አልባ መሆን “መልክዓ ምድራዊ እስር ቤት” እንደሆነና ይህ ሁኔታ ኢትዮጵያን በ24 ዓመታት ውስጥ ልታስመዘግብ የምትችለውን ዕድገት ወደ 36 ዓመታት እንደሚያጓትተው በማስረጃ አሳይተዋል። ይህም የኢትዮጵያን የባሕር በር ጥያቄ ከስሜታዊነት ይልቅ በዓለም አቀፍ የሕግ መርሆዎች እና በታሪካዊ እውነታዎች ላይ የተመሰረተ እንዲሆን ገፊ ምክንያት መሆኑን አትተዋል።
በታሪክ ረገድ ኢትዮጵያ ከአክሱም ሥልጣኔ ጀምሮ የቀይ ባሕር ባለቤት እንደነበረች የሚጠቅሱት ፕሮፌሰር ያዕቆብ፣ የአሰብ ወደብም ቢሆን በታሪክ የአፋር ሕዝብ መኖሪያ እንጂ የኤርትራ አካል ሆኖ እንደማያውቅ ይከራከራሉ። እ.አ.አ በ1889 አሰብ ለጣሊያን ኩባንያ የተሸጠው በአካባቢው በነበረ የአፋር መሬት ባለቤት መሆኑን እና ንጉሠ ነገሥት ምኒልክም በወቅቱ በነበረው የግንኙነት መጓተት ምክንያት ሽያጩን አለማወቃቸውን መጽሐፉ ያብራራሉ። ከዚህም ባለፈ የኤርትራ ደጋማ ክፍል ነዋሪዎች አሰብ ሲሸጥ ተቃውሞ አለማሰማታቸው አካባቢው የኤርትራ አካል ተደርጎ እንደማይታይ አንዱ ማሳያ ተደርጎ እንደሚወሰድ ይጠቅሳሉ።
ከሕጋዊ ሰነዶች አንጻር በ1900፣ በ1902 እና በ1908 በኢትዮጵያ እና በጣሊያን መካከል የተፈረሙት የቅኝ ግዛት ውሎች አሰብን በተመለከተ ግልጽነት የጎደላቸው መሆናቸውን ፕሮፌሰሩ ያዕቆብ ይሞግታሉ። በተለይም የባሕር ዳርቻውን ተከትሎ 60 ኪሎ ሜትር ወደ ውስጥ የሚሰመረው የ1908ቱ ውል፣ የአሰብን አካባቢ እና ወደቡን በግልጽ እንደማያካትትና ወደ ደቡብም በበቂ ሁኔታ እንዳልተዘረጋ የሕግ ባለሙያዎች ይጠቅሳሉ።
ከዚህም በተጨማሪ የጣሊያን በ1928 ዓ.ም ዳግም ኢትዮጵያን መውረር የቀድሞ ውሎችን ሁሉ ውድቅ የሚያደርግ “መሰረታዊ የውል ጥሰት” (Material Breach) በመሆኑ፣ ጣሊያን በ1947 በፈረመችው የሰላም ስምምነት የቅኝ ግዛት ይገባኛል ጥያቄዋን ማቋረጧ ለኢትዮጵያ ጥያቄ ሕጋዊ መሠረት ይሆናል ይላሉ ፕሮፌሰር።
ሌላው እጅግ ወሳኝ የሆነው ሕጋዊ መከራከሪያ በአልጀርሱ ስምምነት አፈጻጸም ላይ የታየው የሕገ-መንግሥት ጥሰት ነው ። የኢትዮጵያ ፓርላማ ስምምነቱን አጸደቀ የተባለው ኅዳር 29 ቀን 1993 ዓ.ም ሲሆን፣ ስምምነቱ ግን በሁለቱ ሀገራት መንግሥታት የተፈረመው ከአራት ቀናት በኋላ ታኅሣሥ 3 ቀን ነበር። ይህ ከመፈረሙ በፊት መጽደቁ በዓለም አቀፍ የውል ሕግ መሰረት የሀገሪቱን ፈቃድ ዋጋ ቢስ ሊያደርገው እንደሚችል እና በድንበር ኮሚሽኑ ውሳኔ ላይ ጥርጣሬ እንደሚፈጥር ፕሮፌሰር ያዕቆብ እና ሌሎች ምሁራን ያስረዳሉ።
በተጨማሪም እ.ኤ.አ በ1884 የተደረገው የሂወት (Hewett) ውል ኢትዮጵያ ወደ ባሕር የመድረስ መብት እንዳላት መደንገጉ እና በ1952 የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት በውሳኔ ቁጥር 390 (A) ኤርትራን ከኢትዮጵያ ጋር ሲያዋህድ የኢትዮጵያን የባሕር በር አስፈላጊነት ዕውቅና መስጠቱ ለጥያቄው ተጨማሪ ሕጋዊ ክብደት ይሰጡታል።
የጥንት የቅኝ ግዛት ድንበሮችን የማክበር መርሕ በኢትዮጵያ እና በኤርትራ ጉዳይ ላይ ተፈጻሚነት የለውም የሚለው የፕሮፌሰር ያዕቆብ መከራከሪያ ለጥያቄው ሕጋዊነት ብቻ ወሳኝ እንደሆነ ይጠቅሳል። ኤርትራ ነጻነቷን ያገኘችው ከኢትዮጵያ እንጂ ከቅኝ ገዥ ሀገር ባለመሆኑ እና እ.አ.አ በ1964 የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የድንበር መርሕን ሲያጸድቅ ኤርትራ የኢትዮጵያ አካል ስለነበረች፣ የኢትዮጵያ ቋሚ ድንበር የባሕር ዳርቻውን የሚያካትት መሆን አለበትም ይላሉ ፕሮፍሰር ያዕቆብ።
ስለሆነም የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ የፍትሃዊነት፣ የታሪካዊ ባለቤትነት እና የቀጣናዊ ትብብር ማዕከል ተደርጎ ሊወሰድ የሚገባው የሕግ ጥያቄ እንደሆነ አስምረውበታል።
#Ethiopia #RedSea #AssabPort #InternationalLaw #HornOf Africa #EconomicSovereignty