የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በ24ኛ መደበኛ ስብሰባው የጉምሩክ አዋጅን ለማሻሻል የቀረበውን ረቂቅ አዋጅ መርምሮ አፅድቋል።
በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ደሳለኝ ወዳጀ ሪፖርት እና የውሳኔ ሀሳብ ለምክር ቤቱ አቅርበዋል።
ረቂቅ አዋጁ የኮንትሮባንድ ንግድን ለመከላከል የሚደረገውን ጥረት በማጠናከር ረገድ ጉልህ ሚና እንዳለው ሰብሳቢው ገልጸዋል።
ረቂቅ አዋጁ በዘርፉ ሀገራችን ከፈረመቻቸው ዓለም አቀፍ ስምምነቶች ጋር የተጣጣመ እንዲሆን የሚያስችል ሲሆን፣ በጉምሩክ አሠራር ውስጥም ፍትሃዊነት እንዲረጋገጥ ምቹ ሁኔታ የሚፈጥር መሆኑ ተገልጿል።
በተጨማሪም፣ ረቂቅ አዋጁ በሀገራችን እያደገ የመጣውን የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ልማት የሚደግፍ እንዲሁም ኢንቨስትመንትን የሚያበረታታ መሆኑን የኮሚቴው ሰብሳቢ አመላክተዋል።
ረቂቅ አዋጁ በነባሩ አዋጅ ውስጥ የተደነገጉ ገደቦችን በተግባር ላይ ሲውሉ ይስተዋሉ የነበሩ የአተገባበር ችግሮችን ለመቅረፍ ያስችሉ ዘንድ አስፈላጊ ድንጋጌዎችን ያካተተ መሆኑንም አንስተዋል።
አስመጪዎች በቀረጥ እና ታክስ አወሳሰን ላይ ያላቸውን አቤቱታ በማቅረብ ሂደት ያጋጥሟቸው የነበሩ የአሠራር መሰናክሎችን ለማስወገድ የሚያስችሉ ድንጋጌዎችን ያካተተ ረቂቅ አዋጅ መሆኑን ጠቁመዋል።
የምክር ቤት አባላት በበኩላቸው፣ በረቂቅ አዋጁ ዝግጅት ወቅት የተከናወነው ሥራ አስፈላጊውን የሕግ ምርመራ እና ግምገማ ሂደት የተከተለ መሆኑን እና አዋጁም በተገቢው ሁኔታ ታይቶ እና ተገምግሞ የቀረበ መሆኑን ገልጸዋል።
በኮንትሮባንድ ጭነት ምክንያት ተሽከርካሪ እንዲወረስ የሚያስችል ድንጋጌ ቢኖርም፣ ባለቤቱ በድርጊቱ ተሳታፊ ባልሆነበት ሁኔታ ንብረቱ ሊወረስ እንደማይገባም አንሥተዋል።
ባለቤቱ ተሽከርካሪውን አሽከርካሪ እንዲጠቀምበት በውል ሲያስረክብ፣ ታማኝና ለሕግ ተገዥ የሆነ ሹፌር መቅጠር እንዲሁም ለሚደርስ ጉዳት ወይም ሕገ-ወጥ ድርጊት ተገቢ ዋስትና መውሰድ እንዳለበት ተጠቁሟል።
ምክር ቤቱ በረቂቅ አዋጁ ላይ ሰፊ ውይይት ካደረገ በኋላ፣ የጉምሩክ አዋጅን እንደገና ለማሻሻል የቀረበ ረቂቅ አዋጅን፣ አዋጅ ቁጥር 1425/2018 አድርጎ በሁለት ተቃውሞ በአብላጫ ድምፅ ማፅደቁን ከምክር ቤቱ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።