Search

በ10 ወራት ከወጪ ንግድ 8.7 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ተገኝቷል - የገንዘብ ሚኒስቴር

ሓሙስ ሰኔ 04, 2018 50

ኢትዮጵያ 2018 በጀት ዓመት 10 ወራት ከወጪ ንግድ 8.7 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቷን የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አሕመድ ሽዴ ገለጹ።

ይህ ገቢ ከባለፈው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር 38.9 በመቶ ዕድገት ማሳየቱን ሚኒስትሩ ተናግረዋል።

የመካከለኛው ምሥራቅ ቀውስ ጫናዎችን በመቋቋም የተገኘው ገቢ 8.7 ቢሊዮን ዶላር የበጀት ዓመቱ ሲጠናቀቅ 10.5 ቢሊዮን ዶላር እንደሚመዘገብ መገመቱን በዛሬው ዕለት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባቀረቡት የበጀት መግለጫ ገልጸዋል።

እየተገባደደ ባለው በጀት ዓመት 10 ወራት ኢትዮጵያ ወደ ሀገር ውስጥ ያስገባቻቸው የገቢ ንግድ 18.4 ቢሊዮን ዶላር መሆኑን የገለጹት ሚኒስትሩ፣ ይህም 2017 በጀት ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር 17.9 በመቶ ዕድገት እንዳለው ተናግረዋል።

የፌዴራል መንግሥት 2019 በጀት ዓመት ረቂቅ በጀት ውሳኔ ቁጥር 24/2018 ሆኖ ለፕላን በጀት እና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ መመራቱን ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።