በሲዳማ ክልል የምግብ ዋስትናን የሚያረጋግጡ እና ገበያን የሚያረጋጉ የግብርና ልማት ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ እና ለዚህም ባለፉት ዓመታት በተሰራው ሥራ ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለጹ።
አቶ ደስታ በሐዋሳ ከተማ እየተካሄደ ክልል አቀፍ የመኸር እርሻ ንቅናቄ መድረክ ላይ እንደገለጹት የግብርና ምርታማነቱን ለማሳካት ከበልግ ምርቱ መሰብሰብ ጎን ለጎን የመኸር ሰብልን ውጤታማ ለማድረግ በትኩረት ይሠራል።
በዚህም የቤተሰብ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ ትርፍ አምርቶ ገበያን ለማረጋጋት እና የኑሮ ውድነትን ተፅዕኖ ለመቀነስ ለሚያስችሉ የግብርና ልማት ሥራዎች ትኩረት እንደሚሰጥ ተናግረዋል።
በምርት ዘመኑ የተያዘውን ዕቅድ ለማሳካትም በየደረጃው ያለ አመራር የኅብረተሰቡን አቅም በማስተባበር ለውጤቱ በትጋት መሥራት እንዳለበትም ማሳሰባቸውን ኢዜዘ ዘግቧል።
የክልሉ እርሻ እና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ መምሩ ሞኬ በበኩላቸው፣ በዘንድሮው የመኸር እርሻ ከ169 ሺህ ሔክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች እንደሚለማ ተናግረዋል።
በዚህም ከ16 ነጥብ 5 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ ጠቁመዋል።