የአረንጓዴ አሻራ ንቅናቄ ለኢትዮጵያ የደን ሽፋን እድገት፣ ለምግብ ዋስትና እና ለአየር ንብረት ለውጥ መከላከል እያበረከተ ያለው አስተዋጽኦ ከፍተኛ ነው።
ላለፉት ሰባት ዓመታት የተመዘገቡት ስኬቶች እና የትናንት ጥንካሬያችን ደግሞ ለዚህ ማሳያዎች ናቸው፡፡
2011 ዓ.ም ንቅናቄው በይፋ የተጀመረበት ሲሆን፤ ከተቀመጠው የ4 ቢሊዮን የችግኝ ተከላ ግብ በላይ በማሳካት ደማቅ ስኬት በማስመዝገብ ተጀምሯል።
2012 ዓ.ም ዓለምን በፈተነው የኮቪድ-19 ወረርሽኝ ወቅትም የንቅናቄው ቀጣይነት ተረጋግጦ 5.7 ቢሊዮን ችግኞች ተተክለዋል።
2013 ዓ.ም የማኅበረሰብ ተሳትፎን እና ሀገራዊ አንድነትን ያጠናከረ ተከላ ተከናውኗል፡፡ በዚህም 6.8 ቢሊዮን ችግኞችን ለመትከል ተችሏል።
2014 ዓ.ም የምዕራፍ 1 ማጠቃለያ ላይ 7.2 ቢሊዮን ችግኞች የተተከሉ ሲሆን፣ በአጠቃላይ በምዕራፉ ከ25 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን መድረስ ተችሏል።
2015 ዓ.ም የምዕራፍ 2 ጅማሮ ነበር፡፡ ትኩረቱ በኢኮኖሚያዊ፣ የግብርና እና የፍራፍሬ ችግኞች ላይ በማድረግ 7.5 ቢሊዮን ችግኞች ተተክለዋል።
2016 ዓ.ም የተተከሉ ችግኞችን የጽድቀት መጠን ለመከታተል የካርታ ሥራ (Geo-spatial tracking) እና የጥራት ክትትል ሥራዎች በይፋ ተጀምረዋል፡፡ በዚህ ዓመትም 7.5 ቢሊዮን ችግኞች ተተክለዋል።
2017 ዓ.ም "በመትከል መታደስ" በሚል መሪ ቃል በአንድ ጀምበር (በ12 ሰዓታት ውስጥ) 714.7 ሚሊዮን ችግኞች ተተክለው አዲስ የዓለም ክብረ ወሰን ተሰብሯል። በዓመቱም 7.5 ቢሊዮን ችግኝ ማሳካት ተችሏል።
ይህ የሰባት ዓመቱ ስኬት ሀገራዊ አንድነታችንን እና የአፈጻጸም ብቃታችንን የሚያሳይ ሲሆን፣ የዘንድሮው የ2018 ዓ.ም የ8 ቢሊዮን ችግኝ ተከላ እቅድ ደግሞ ንቅናቄው ሳይቀዘቅዝ ይበልጥ እየተጠናከረ መሄዱን ማሳያ ነው፡፡
እስከ አሁን በመጣንበት ሂደት ከ48 ቢሊዮን ችግኞች በላይ መትከል የተቻለ ሲሆን፣ ዘንድሮ 8 ቢሊዮን በመጨመር አጠቃላይ ሀገራዊ የችግኝ ተከላ መጠኑን ወደ 56 ቢሊዮን ለማድረስ ዝግጅት ተጠናቅቋል።
በተጠናከረ የሕዝብ ተሳትፎ ከተተከሉት ችግኞች የጽድቀት መጠኑ ከ80 በመቶ በላይ መድረሱ ደግሞ የልፋታችን ትልቁ ትሩፋት ነው፡፡
በቢታኒያ ሲሳይ