ባለፉት ሰባት ዓመታት በአረንጓዴ ዐሻራ ንቅናቄ አስደማሚ ስኬቶችን ያስመዘገበችው ኢትዮጵያ አሁን ላይ "ተስፋን እንትከል" በሚል ሀገራዊ መሪ ሐሳብ ግቧን ከ56 ቢሊዮን በማድረስ አዲስ የዓለም ታሪክ ለመጻፍ የመጨረሻው ምዕራፍ ላይ ትገኛለች።
በሰባት ዓመታት ብቻ ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን በመትከል ያለፈውን የመሬት መራቆት ጠባሳን ለመሻር የሚያስችል ትልቅ መሠረት ጥላለች።
በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነትና በ"መደመር" ፍልስፍና የተቀረጸው ይህ ብሔራዊ መርሐ ግብር ቀደም ሲል የነበረውን የአካባቢ መራቆት እና የደን መመናመን ጠባሳ በመሻር ረገድ ከፍተኛ ውጤት እያስመዘገበ ይገኛል።
በዚህም በየጊዜው እያሽቆለቆለ ወደ 3 በመቶ ዝቅ ብሎ የነበረው የደን ሽፋን ባለፉት ሰባት ዓመታት በተከናወነው የተቀናጀ ርብርብ ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞች ተተክለው ለውጥ መታየት ጀምሯል።
የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር ከ767 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች አዲስ የሥራ ዕድል መፍጠር ችሏል፤ የአፈር መሸርሸርንም በከፍተኛ ሁኔታ ቀንሷል።
መርሐ ግብሩ ከታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ እና መሰል ሜጋ ፕሮጀክቶችን ከደለል ከመታደግ ባለፈ በግብርናው ዘርፍ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ እንዲሁም ለኢንዱስትሪዎች ጥሬ ዕቃ ለማቅረብ ትልቅ መሠረት እየጣለ ይገኛል።
ዘንድሮም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) “ተስፋን እንትከል” በሚል መሪ ሐሳብ የተጀመረው የ8ኛው ዓመት የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር ለቀጣዩ ትውልድ የበለጸገችና አረንጓዴ የሆነች ኢትዮጵያን ለማውረስ የሚደረግ ሁለንተናዊ የብልፅግና ጉዞ አካል ነው።
በቢታኒያ ሲሳይ