ዲፕሎማሲ በባዶ ሜዳ ላይ በሚዘራ የመልካም ወዳጅነት እና የፈገግታ ልውውጥ ብቻ የሚገነባ አይደለም። ይልቁንም፣ አንድ አገር በዓለም አቀፍ መድረክ ላይ ተደማጭነት እና ተፅዕኖ ማምጣት የምትችለው በቅድሚያ ጠንካራ ውስጣዊ አቅም ስትገነባ ነው። ጠንካራ ዲፕሎማሲ ከጠንካራ ውስጣዊ አንድነት፣ ሰላም፣ የሕግ የበላይነት እና መልካም አስተዳደር እንደሚጀምር የሀገራችን የውጭ ግንኙነት ዕሳቤ በግልጽ ይገነዘባል።

ኢትዮጵያም የውጭ ግንኙነቷን በአንድ ኃያል ወገን ደጋፊ መሆን ላይ ብቻ ሳታንጠለጥል፣ ለራሷ ኃያል መሆንን ማዕከል በማድረግ ውስጣዊ አቅሟን አፈርጥማለች። ኢትዮጵያ በልጆቿ ላብ፣ በውስጥ አቅሟና በፅኑ ጥረቷ ራሷን እየቀየረች የዓለምን ዲፕሎማሲ ወደ ራሷ መሳብ የቻለችውም ለዚህ ነው።

ባለፉት የለውጥ ዓመታት ሀገራችን የተከተለችው መደመራዊና ፍፁማዊ ሀገራዊ ጥቅምን ያስቀደመ የውጭ ግንኙነት ዕሳቤ፣ ኢትዮጵያን ከጂኦስትራቴጂያዊ ኩስመና በማላቀቅ የዓለም ኃያላን ዓይን የሚያርፍባት አንከር አገር አድርጓታል። የዓለም አይኖች ሁሉ ወደ ኢትዮጵያ ያረፉበትን ዋና ዋና ምክንያቶች በጥልቀት ስንመለከት የሚከተሉት ጎልተው ይወጣሉ፡-
1. አዲስ አበባ፡ የዓለም የዲፕሎማሲ ቁልፍ ማዕከል
አዲስ አበባን እውንና ምርጥ በማድረግ ረገድ የተሰሩት የከተማ ልማትና ማስዋብ እንዲሁም የኮሪደር ልማት ስራዎች ከተማዋን የዓለም የዲፕሎማሲ መስህብ አድርገዋታል። የኮንፈረንስ ቁሳዊና ሰብዓዊ መሰረተ ልማቶችን በማስፋፋት፣ በአንድ ዓመት (በ2017 በጀት ዓመት) ውስጥ ብቻ ከ150 በላይ ዓለም አቀፍ ኮንፈረንሶችን በብቃት ማስተናገድ መቻሏ የዓለምን ትኩረት በከፍተኛ ሁኔታ ስቧል።
2. ለአካባቢ ተስማሚ (Environmentally Friendly) ኢኮኖሚ ግንባታ
ሀገራችን የተፈጥሮ ሀብቷን በመጠበቅና አረንጓዴ ኢኮኖሚን በመገንባት ያሳየችው ቆራጥነት ዓለም አቀፍ እውቅናን አግኝቷል።
በአረንጓዴ አሻራ ዲፕሎማሲ ባስመዘገበችው አስደናቂ ውጤት ምክንያት ከ75,000 በላይ ተሳታፊዎች የሚገኙበትን የዓለም የአየር ንብረት ለውጥ ጉባዔ (COP32) እንድታዘጋጅ ተመርጣለች።
በስንዴ ምርት እምርታዊ ለውጥ በማምጣት የምግብ ሉዓላዊነቷን ማረጋገጧ የዓለም መሪዎችን አድናቆት አስገኝቶላታል።
የተፈጥሮ ሀብቷን በማልማትና የታዳሽ ኃይል አቅርቦቷን ማሳደጓ ኢትዮጵያን ወደ ዘላቂና አረንጓዴ ዕድገት መርቷታል።
3. ሚዛናዊ (ከወገንተኝነት የተላቀቀ) ዲፕሎማሲ እና የሰላም ዘብነት
ኢትዮጵያ በአንድ ኃያል ወገን ደጋፊነት ላይ ሳትመሰረት፣ ነፃና ሚዛናዊ የሆነ የዲፕሎማሲ አቅጣጫን ትከተላለች። በዓለምም ሆነ በቀጠናው ሰላም በፅናት በመቆም ትልቅ ሚና እየተጫወተች ትገኛለች።
በሱዳን የተከሰተውን ቀውስ ለመፍታት "አፍሪካዊ መፍትሄ ለአፍሪካዊ ችግሮች" በሚል መርህ የአሸማጋይነት እና የመሪነት ሚና ተጫውታለች።
በሶማሊያ ዘላቂ ሰላምና መረጋጋት እንዲሰፍን የሰላም ማስከበር ተልዕኮዋን አጠናክራ በመቀጠል ለቀጠናው ደኅንነት ያላትን ጽኑ አቋም አሳይታለች።
4. በጋራ ጥቅም ላይ የተመሰረተ ትስስር
"ሰጥቶ-መቀበል" በሚለው መርህ ላይ በመመስረት ከጎረቤት ሀገራት ጋር የፈጠረችው የኢኮኖሚ፣ የንግድ እና የመሰረተ ልማት ትስስር ለቀጠናዊ ውህደት ትልቅ አብነት ሆኗል። ለጂቡቲ፣ ለኬንያ እና ለሱዳን የኃይል አቅርቦት በማቅረብ የፈጠረችው የጋራ ተጠቃሚነት ትስስር ኢትዮጵያን የቀጠናው የኢኮኖሚ ምሰሶ እንድትሆን አድርጓታል።
5. አጋርነትን ማብዛት እና የBRICS አባልነት
የሀያላንን ፉክክር በጥንቃቄ በማስተዳደር እና አዳዲስ ወዳጆችን በማብዛት ያደረገችው ጥረት የዓለምን የኢኮኖሚ ሚዛን እየቀየረ ባለው የBRICS ስብስብ ሙሉ አባል እንድትሆን አስችሏታል። ይህ ታሪካዊ አባልነት የኢትዮጵያን ተደማጭነት ከፍ ከማድረጉም በላይ፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ ያላትን የዲፕሎማሲ አቅምና የስትራቴጂካዊ ተወዳዳሪነት አረጋግጧል።