ባለፉት ጥቂት ዓመታት ብቻ ኢትዮጵያ በዲፕሎማሲው መስክ አሸናፊ የሆነችበት እውነተኛ ሚስጥር ምንድን ነው?
· ከከበባ ስነ-ልቦና (Siege Mentality) እና ከርዕዮተ-ዓለማዊ እስረኝነት ወደ ዓለም አቀፍ ተደማጭነት፡ የኢትዮጵያ ታሪካዊ የዲፕሎማሲ ትንሣኤ!
· የውሃ ጂኦ-ፖለቲካዊ ጫናን የሰበረ፣ የባሕር በር ውግዝነት የገፈፈ እና የብሪክስ (BRICS) በሮችን ያስከፈተ ገቢር-ነበብ ስትራቴጂ!
የአንድ አገር የውጭ ግንኙነት እና ዲፕሎማሲያዊ ስኬት የሚለካው ብሔራዊ ጥቅሟን፣ ሉዓላዊነቷን እና ሁለንተናዊ ልዕልናዋን በተለዋዋጭ የጂኦ-ፖለቲካዊ አውድ ውስጥ ለማስጠበቅ በሚኖራት ስትራቴጂካዊ ተለማጭነት ነው። ኢትዮጵያ ለዘመናት የቆየ የመንግሥትነት ታሪክ ያላትና የዓለም አቀፍ ተቋማት መሥራች ብትሆንም፣ የዲፕሎማሲ ጉዞዋ በተለያዩ ታሪካዊ ማነቆዎች ሲፈተን ቆይቷል።
ቀደም ባሉት ሥርዓታት ዲፕሎማሲው ከብሔራዊ ጥቅም ይልቅ ለሥርዓት ህልውና ቅድሚያ የሰጠ፣ በ"ከበባ ስነ-ልቦና" (Siege Mentality) የታሰረ፣ እና ምዕራባውያን ያሰመሩትን መስመር አስፈፃሚ (Proxy) ወደ መሆን ያዘነበለ ነበር።
ከለውጡ ወዲህ የተመዘገበው አንፀባራቂ የዲፕሎማሲ አሸናፊነት ምስጢር የሚመነጨው ከተቸካይ ርዕዮተ-ዓለማዊ እስረኝነት በመላቀቅ ነው። "መደመር" የፉክክርና የትብብር እሴቶችን በማጣመር ሚዛናዊ የዲፕሎማሲ መንገድን ከፍቷል።
ልክ እንደ ህንድ እና ቱርክ ያሉ ታዳጊ ኃያላን አገራት በባለብዙ ዋልታ (Multipolarity) የዓለም ሥርዓት ውስጥ ተግባራዊ እንደሚያደርጉት ሁሉ፣ ኢትዮጵያም ከምሥራቅም ሆነ ከምዕራብ የኃይል ጎራ ሥር ራሷን ሳታስገባ፣ "ባለብዙ አሰላለፍ" (Multi-alignment) እና "ስትራቴጂካዊ ማመጣጠን" (Strategic Hedging) መርሆዎችን በመከተል ጂኦ-ፖለቲካዊ ነፃነቷን አረጋግጣለች።

ይህ ተግባራዊ (Pragmatic) ዕሳቤ አገሪቱን ወደ ላቀ ጂኦ-ፖለቲካዊ አውድ አሸጋግሯታል፡-
የውሃ ዲፕሎማሲ እና ቀጠናዊ ውህደት፡ ታላቁን የህዳሴ ግድብ በውጭ ጫናዎች ሳይበገር በድል ማጠናቀቅ መቻሉ የኢትዮጵያን የበላይ ትርክት አፅንቷል ፡፡ ከዚህም ባሻገር የአባይ ወንዝ የተፋሰስ የትብብር ማዕቀፍ ስምምነት (CFA) በይፋ ወደ ሥራ መግባቱ የቀጠናውን የሃይድሮ-ፖለቲካዊ ጫና የሰበረ ታሪካዊ ድል ነው።
የባሕር በር የህልውና ጥያቄ፡ ለሠላሳ ዓመታት በታቦ (Taboo) ደረጃ ታፍኖ የነበረውን የባሕር በር እና የወደብ ባለቤትነት መብት ጥያቄ በድፍረት ወደ ዓለም አቀፍ መድረክ በማምጣት ፍትሐዊ መፍትሔ ለማግኘት እየተሰራ ይገኛል።
የብሪክስ (BRICS) አባልነት፡ ከ40 በላይ አገራት በጠየቁበት ፉክክር ውስጥ ኢትዮጵያ የBRICS ሙሉ አባል መሆኗ የዓለም አቀፍ ተደማጭነቷን እና የድርድር አቅሟን ወደ ላቀ ደረጃ አድርሶታል።

የኢኮኖሚ እና ዜጋ-ተኮር ዲፕሎማሲ፡ 4 ቢሊዮን ዶላር የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት በመሳብ እና የወጪ ንግድን ወደ 8.3 ቢሊዮን ዶላር በማሳደግ ኢኮኖሚን ማዕከል አድርጋለች ፡፡ ዜጋ-ተኮር ዲፕሎማሲን በማስፋፋት ለ503,000 ዜጎች ሕጋዊ የሥራ ዕድል ተፈጥሯል፤ ከ500,000 በላይ በችግር ውስጥ የነበሩ ዜጎችም በክብር ተመልሰዋል።


የዓለም አቀፍ ኮንፈረንስ እና አረንጓዴ አሻራ፡ በአንድ ዓመት ብቻ ከ150 በላይ ዓለም አቀፍ ኮንፈረንሶችን በማስተናገድ የአፍሪካ ማዕከልነቷን አጠናክራለች ፡፡ የአረንጓዴ አሻራ እና የግብርና ስኬትም የCOP32 አዘጋጅነትን እና ዓለም አቀፍ የFAO ሽልማቶችን አስገኝቶላታል።

በመሆኑም የኢትዮጵያ የዲፕሎማሲ አሸናፊነት የዕድል ውጤት ሳይሆን፣ የውስጥ አቅምን ለውጫዊ ዲፕሎማሲያዊ ተፅዕኖ ፈጣሪነት ማዋል መቻሏ ነው። የውስጥ የመፈፀም አቅም በቀጥታ ወደ የመደራደሪያ ጉልበት ተቀይሯል። በቀጣይም ይህን የተጀመረውን ዘመናዊ፣ ሚዛናዊ እና ብሔራዊ ጥቅምን ያማከለ ገቢር-ነበብ የዲፕሎማሲ መስመር በተቋማዊ ጥንካሬ አስጠብቆ መሄድ፣ የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ የጂኦ-ስትራቴጂካዊ ልዕልና በዘላቂነት ለማረጋገጥ ወሳኝ መሠረት ይሆናል።