የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን ከሐምሌ 8 ቀን 2018 ዓ.ም. ጀምሮ ለሚያካሂደው ታላቁ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ የመጨረሻ ምዕራፍ ዝግጅት መጀመሩን አስታወቀ።
ጉባኤውን ለሚመሩ አመካካሪ ምሁራን የሚሰጥ የሥራ መመሪያና የሰባት ቀናት የክህሎት ሥልጠና በአዲስ አበባ ኃይሌ ግራንድ ሆቴል በዛሬው ዕለት ተጀምሯል።

የኮሚሽኑ ሰብሳቢ ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ በሥልጠናው መክፈቻ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት፤ ይህ የምክክር ሂደት በኢትዮጵያ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የሚደረግና ለሀገረ-መንግሥት ግንባታ እንዲሁም ለማኅበራዊ ስምምነት መሠረት የሚጥል መሆኑን ገልጸዋል።
ኮሚሽኑ እስካሁን በሁሉም የኢትዮጵያ አካባቢዎች ሕዝባዊ አጀንዳዎችን በስፋት ሲያሰባስብ መቆየቱንና አሁን ላይ ሁሉንም ያካተተ የምክክር መድረክ ለመጀመር በዝግጅት ላይ መሆኑን ጠቁመዋል።
በዚህ ታሪካዊ ሥልጠና ላይ ከተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍሎች የተወከሉ ምሁራን የተሳተፉ ሲሆን፣ ከስዊድንና ከኔዘርላንድስ በመጡ ዓለም አቀፍ ባለሙያዎች አማካኝነት የክህሎት ማሳደጊያ ሥልጠና ይሰጣቸዋል።


ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ ምሁራኑ የተጣለባቸውን ይህንን ታሪካዊና ሀገራዊ ኃላፊነት በብቃት እንዲወጡ ጥሪ ያቀረቡ ሲሆን፤ ኮሚሽኑ በሀገር አቀፍ ደረጃ ምክረ-ሀሳብ የሚያሰናዳበትን ታላቁን ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ በሐምሌ 8 ቀን በአዲስ አበባ ከተማ ለመጀመር የመጨረሻ ምዕራፍ ዝግጅቱን እያጠናቀቀ እንደሚገኝ ታውቋል።