የኢፌዴሪ ገንዘብ ሚኒስትር አቶ አሕመድ ሽዴ ከዓለም ባንክ የኦፕሬሽንስ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አና ብጄርዴ ጋር ተገናኝተው በነበራቸው ቆይታ፣ ኢትዮጵያ እያስመዘገበችው ስላለው ቀጣይነት ያለው የሪፎርም እንቅስቃሴና መንግሥት በትኩረት እየሠራባቸው ስላሉት ዋነኛ አቅጣጫዎች ሰፊ ገለጻ አድርገውላቸዋል።
ሚኒስትሩ አክለውም በቀጣይ በሚቀረጸው የኢትዮጵያና የዓለም ባንክ ስልታዊ የአጋርነት ማዕቀፍ ውስጥ ቅድሚያ ሊሰጣቸው በሚገቡ ስልታዊና መዋቅራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ዝርዝር ማብራሪያ ሰጥተዋል።
የዓለም ባንክ የኦፕሬሽንስ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አና ብጄርዴ በበኩላቸው፣ የኢትዮጵያ መንግሥት የጀመረውን ጠንካራ የኢኮኖሚ ማሻሻያ ትግበራና እያስመዘገበ ያለውን ተስፋ ሰጪ አዎንታዊ የኢኮኖሚ ለውጦች አድንቀዋል።
ይህንኑ የተሳካ የሪፎርም አጀንዳ ይበልጥ ለማገዝና ኢትዮጵያ ያስቀመጠቻቸውን የረጅም ጊዜ የልማት ግቦች ዳር ለማድረስ ባንኩ እያደረገ ያለውን ሁለንተናዊ ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ማኔጂንግ ዳይሬክተሯ በውይይቱ ወቅት አረጋግጠዋል።
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: