Search

በ2019 በጀት ዓመት ከቡና ወጪ ንግድ 4 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ለማግኘት ታቅዷል - የግብርና ሚኒስትር አዲሱ አረጋ

ማክሰኞ ሐምሌ 14, 2018 84

የግብርና ሚኒስትሩ አቶ አዲሱ አረጋ ከፍተኛ ጥራት እና ዋጋ ያለው ቡና ለማምረት በሳይንሳዊ አሠራር ላይ የተመሰረተ እንክብካቤ ማድረግ ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል።

ኢትዮጵያ 2018 በጀት ዓመት ከቡና ኤክስፖርት 3 ነጥብ 1 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር ገቢ በማስገኘት አዲስ ታሪክ ማስመዝገቧን ያስታወሱት ሚኒስትሩ፤ ይህ ስኬት የተመዘገበው ከቡና ምርት እስከ ዝግጅት እንዲሁም ለዓለም አቀፍ ገበያ እስከማቅረብ ድረስ በተሠራው የተቀናጀ ሥራ እና የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር በፈጠረው ምቹ ሁኔታ መሆኑን አስታውቀዋል።

2019 በጀት ዓመት እንደ ሀገር 550 ሺህ ቶን ቡና ለውጭ ገበያ በመላክ 4 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር ገቢ ለማግኘት መታቀዱን ሚኒስትሩ አመልክተዋል።

ለዚህ እቅድ መሳካት የቴክኖሎጂ አጠቃቀምና በቂ እንክብካቤ ወሳኝ መሆኑን ያነሱት አዲሱ፣ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል በጉራፈርዳ እና በደቡብ ቤንች ወረዳዎች የሚገኘውን እና በሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ስር የሚተዳደረውን የባበቃ ቡና ልማት ድርጅት በምሳሌነት ጠቅሰዋል።

ድርጅቱ ካለው 10 ሺህ ሄክታር መሬት ውስጥ 5 ሺህ 677 ነጥብ 64 ሄክታሩ በቡና የተሸፈነ ሲሆን፣ ልማቱም በበቂ እንክብካቤ እና በቴክኖሎጂ ተደግፎ በጥሩ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ አብራርተዋል።

በተለይም የዝናብ እጥረት ችግርን ለመፍታት 200 ሄክታር ማሳ ላይ የጠብታ መስኖ ቴክኖሎጂን በመጠቀም እያለሙ መሆኑን እና ይህም አሠራር ከአንድ ሄክታር ይገኝ የነበረውን አማካይ 10 ኩንታል የቡና ምርታማነት በእጥፍ በማሳደግ እስከ 20 ኩንታል እንዲደርስ ማስቻሉን በማኅበራዊ ትስስር ገጽ ባጋሩት መልዕታቸው አስገንዝበዋል።

አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: