በጥሩነሽ ቤጂንግ አጠቃላይ ሆስፒታል የ26 ዓመት ወጣት እናት በአንድ ጊዜ አራት ልጆችዋን በሰላም መገላገሏን የአዲስ አበባ ጤና ቢሮ አስታወቀ።
በአሁኑ ወቅት እናትየዋ እና አራቱ ልጆቿ በጥሩ ጤንነት ላይ እንደገሚኙ ተገልጿል።
የሕክምና ሂደቱን በበላይነት የሰጡት እና የመሩት የሆስፒታሉ ዋና ሥራ አስኪያጅ እና የማህፀን እና ፅንስ ስፔሻሊስት የሆኑት ዶክተር የሆኑት እሸቱ ታደለ እና ሌሎች የሆስፒታሉ የሕክምና ቡድን ቀዶ ሕክምናውን በስኬት ማጠናቀቁን አስታውቀዋል።
ዶክተር እሸቱ ስለ ሕክምናው ዝርዝር ሁኔታ ሲያብራሩ፣ አራት ሕፃናትን በአንድ ጊዜ በሰላም ማገላገል በሆስፒታሉ የመጀመሪያው እንዳልሆነ ገልጸው ከሦስት ዓመት በፊትም በተመሳሳይ አንዲት የ24 ዓመት ወጣት እናት በሪፈር ከጤና ጣብያ ወደሆስፒታሉ ገብታ አራት ሕፃናትን በሆስፒታሉ በሰላም መገላገሏን አስታውሰዋል።
የአሁኑን ለየት የሚያደርገው የ26 ዓመቷ እናት አራት ፅንስ መፀነስዋን በሆስፒታላችን ክትትል በምታደርግበት ወቅት በመታወቁ ለእናቲቱ እና ለሚወለዱት ጨቅላዎች ደኅንነት ከፍተኛ የሆነ ክትትል እንደሚያስፈልግ ከግምት ውስጥ በማስገባት የወሊድ ቀኗ ከመድረሱ ከአንድ ወር በፊት ጀምሮ በዋርድ በማስተኛት ሌት ከቀን ክትትል እንደተደረገላት ተናግረዋል።
በመውለጃ ቀኗም በጨቅላ ሕፃናት ክፍል ለሕፃናቱ ማረፍያ እና አጋዥ ማሽኖች ቅድመ ዝግጅት መደረጉን የገለጹት ዋና ሥራ አስኪያጁ ሆስፒታሉ ተገልጋይ ተኮር አሠራርን ስለሚከተል በከፍተኛ የሕክምና ቴክኖሎጂ እና መሳሪያዎች የተደራጀ በመሆኑ፣ በየዘርፉ ስፔሻላይዝ ያደረጉ ወጣት እና ቁርጠኛ የሕክምና ባለሙያዎች ስብስብ በመኖሩ አገልግሎቱ በቁርጠኝነት መሰጠቱን ተናግረዋል።
ለእናቶች እና ሕፃናት የተሰጠ ትኩረት እጅግ ከፍተኛ እንደሆነ የገለጹት ዶክተር እሸቱ እንደ አሁኑ አይነት አልፎ አልፎ የሚያጋጥሙና ከፍተኛ ጥንቃቄ የሚሹ እርግዝናዎች በሚከሰቱበት ጊዜ "እናት ጤና፤ ልጅም ደህና" የሚለውን ሀገራዊ የጤና መርሕ በተግባር ለማዋል በትኩረት እየተሠራ መሆኑን የሚያሳይ ተግባር እደሆነም ዋና ስራአስኪያጅ ዶክተር እሸቱ ማብራራታቸውን ከአዲስ አበባ ጤና ቢሮ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: