Search

የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ በዓለም አቀፍ ደረጃ የሰላም ዕውቅና ሽልማት አሸናፊ ሆነ

ማክሰኞ ነሐሴ 26, 2018 113

የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ባለፉት 15 ዓመታት በኢትዮጵያ ሰላምን፣ መከባበርን እና አንድነትን ለማስፈን ላበረከተው አስተዋጽኦ የዓለም አቀፍ የሰላም ዕውቅና ሽልማት አሸናፊ መሆኑ ይፋ ሆነ።

የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ የተመሠረተበትን 15 ዓመት የምሥረታ በዓል ዛሬ በአዲስ አበባ በደመቀ ሁኔታ አክብሯል።

በመድረኩ የዓለም የሃይማኖት እና የባህላዊ ሰላም ግንባታ ኔትዎርክ (Network for Religious and Traditional Peacemakers) ተወካይ ኢትዮጵያ ለሰላም ግንባታ የምታደርገውን ጥረት አድንቀዋል።

ኢትዮጵያ የሰላም ሚኒስቴርን በማቋቋም ለዓለም አርአያ የሚሆን ተግባር ማከናወኗን የጠቀሱት ተወካዩ፣ ይህም ሀገራችን ለሰላም የሰጠችውን ከፍተኛ ትኩረት እና የፖለቲካ ቁርጠኝነት የሚያሳይ ነው ብለዋል። ወቅቱ ዓለም ሰላምን አጥብቃ የምትሻበት በመሆኑ፣ የኢትዮጵያ ተሞክሮ ለሌሎች ሀገራትም ትልቅ ምሳሌ እንደሚሆን ገልጸዋል።

ኢትዮጵያ የነጃሺ ምድር እና የመጀመሪያው የእስልምና ስደት (ሒጅራ) በክብር የተስተናገደባት ሀገር መሆኗን አስታውሰው፣ ሀገራችን ለዘመናት የዘለቀ የማኅበራዊ ትሥሥር፣ የትዕግሥት እና የአብሮነት ተምሳሌት መሆኗንም ምሥክርነታቸውን ሰጥተዋል።

የዓለም የሃይማኖት እና የባህላዊ ሰላም ግንባታ ኔትዎርክ፣ የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ላከናወናቸው ውጤታማ የሰላም ሥራዎች ይህንን የክብር ሽልማት ለመስጠት መወሰኑን ይፋ አድርገዋል። ሽልማቱም ነገ በአፍሪካ ኅብረት አዳራሽ 56 ሀገራት የተወከሉ 120 ድርጅቶች ተወካዮች በተገኙበት በሚካሄደው ዓመታዊ ጉባኤ ላይ በይፋ እንደሚበረከት ነው የጠቆሙት።

ከመቶ በላይ አባላት የሚሳተፉበትን ዓለም አቀፍ የምክክር መድረክ በሰላሟ ምድር፣ በማኅበራዊ ትሥሥር እና በመግባባት ተምሳሌት በሆነችው ኢትዮጵያ በማድረጋችን ታላቅ ክብር ይሰማናልብለዋል።

ይህ ዓለም አቀፍ ኔትዎርክ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የቀድሞ ዋና ጸሐፊ ባን ኪሙን ሪፖርት መሠረት የተቋቋመ ሲሆን፣ በዓለም ዙሪያ ለሰላም ግንባታ እና ለግጭት አወጋገድ የሃይማኖት አባቶች እና የባህላዊ መሪዎች ያላቸውን ጉልህ ሚና ለማጎልበት በንቃት የሚንቀሳቀስ ድርጅት ነው።

የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ለሀገር ሰላም እና አብሮነት ያበረከተው አስተዋጽኦ የላቀ መሆኑ በመድረኩ ተነሥቷል።

በላሉ ኢታላ

አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: