Search

“ሁሉንም ነገር ሰጥቻለሁ፤ ያስቀረሁት ምንም ነገር የለም” - ሊዮኔል ሜሲ

ማክሰኞ ነሐሴ 26, 2018 160

እግር ኳስ ውድ ልጇን እየተሰናበተች ነው። የነገሩ መነሻ 23ኛው ዓለም ዋንጫ ሽንፈት፣ ሕይወቱን ያጎደለው የወላጅ አባቱ ሆርሄ ሜሲ ሕልፈት ወይስ ዕድሜ? ከተባለ መልሱ ሁሉንም የሚል ይሆናል።

በእርግጥ እርሱ ለእግር ኳስ ሁሉንም ነገር ሰጥቷል፤ የሰሰተው አንዳች ነገር የለም የሚለው ለክርክር የሚቀርብ ላይሆን ይችላል።

ሊዮኔል ሜሲ ከላ ማሲያ ተነሥቶ የካታላኑ ኃያል ክለብ ኩራት ብቻ ሆኖ አልቀረም፣ ትዝታው በፈረንሳይ እና አሜሪካ ክለቦች ባሳለፋቸው ዘመናት ብቻ የሚዘጋም አይደለም።

አልበሰልስቴዎችከዲዬጎ አርማንዶ ማራዶና የእግር ኳስም የምድርም ስንብት በኋላ ከድል ጋር ያገናኛቸው፣ ከተስፋ መቁረጥ ዳርቻ የመለሳቸው ውድ ልጃቸው ነው እና ይህን የስንብት ዜና በዋዛ የሚያልፉት አይሆንም።

2014 ከዓለም ሻምፒዮንነት ደጃፍ ላይ ቆመው ጀርመን ስታስቀራቸው፤ 2007 2015 እና 2016 በአህጉራዊው የኮፓ አሜሪካ ውድድር ፍጻሜዎች የዋንጫውን አንድ እጀታ እየጨበጡ አሳልፈው ሲሰጡ መንገዱ ፈተና ገጥሞታል። ይህን ተከትሎ የተሰነዘሩ ትችቶችን ጫንቃው የማይችለው ሆኖ ሲሰማው ገና 29 ዓመቱጉዞው አብቅቷልበማለት ከአርጀንቲና ብሔራዊ ቡድን መሰናበቱን እስከማወጅ ደርሶ ነበር።

በዲዬጎ አርማንዶ ማራዶና ጭምርየመሪነት ስብእናን ያልተላበሰተብሎ ሲተች በቃኝ ቢልም፣ የወቅቱ የአርጀንቲና ፕሬዚዳንት ማውሪዚዮ ማክሪን ጨምሮ በርካቶች ያሰሙትን አስብበትተማጽኖ ሰምቶ፣ ቡድኑን ያላንተ ማሰብ እንዴት ይቻላል ለሚለው ውትወታ እጅ ሰጥቶ ለአርጀንቲና ብሔራዊ ቡድን ዳግም ለመጫወት ወሰነ። የዓለም እግር ኳስም ሌላ ውብ ዐሥር ዓመታት ተጨመረለት።

የኮፓ አሜሪካ እና የምድራችን ትልቁ የእግር ኳስ መድረክ ዓለም ዋንጫ የሻምፒዮንነት ጥያቄዎችም በእነዚያ ዐሥር ዓመታት ተመለሱ። በመውጣት እና መውረድ ውስጥምሀገሬን እና ይህን መለያ በጣም ነው የምወዳቸውእያለ እግር ኳስ ያሉትን ለእርሱ ግን ጎድለውት የነበሩትን ክብሮች ሁሉ ተራ በተራ አሳካ። ለአርጀንቲናም አለኝታ ሆነ።

ሊዮኔል ሜሲ በአርጀንቲና ብሔራዊ ቡድን ሁለት ዐሥርት ዓመታት በተሻገረ ቆይታው 207 ጨዋታዎች 125 ግቦችን አስቆጥሯል፣ 11 ጊዜ ሐትሪክ ሠርቷል። 6 ዓለም ዋንጫዎች 34 ጨዋታዎችን በማድረግም የመጀመሪያው ተጫዋች ተሰኝቷል።

አሁን አዳዲስ ወጣት ኮከቦች እርሱ ባለፈበት የስኬት መንገድ ያልፉ ዘንድ አዲሱን መንገድ መጀመሩን አስታውቋል።ስሰናበት ፍጹም ሰላም እየተሰማኝ፣ ከሁለት ዐሥርት ዓመታት በላቀው መንገዴም እየኮራሁ ነውብሏል።

ከዓለም ዋንጫው ፍጻሜ ሁለት ቀን በኋላ እንደጻፈው ሆኖም በወላጅ አባቱ ኅልፈት ምክንያት እንዳዘገየው በገለጸው የስንብት መልዕክት፣ ውሳኔው ከዚያም አስቀድሞ የደረሰበት እንደሆነ ይፋ አድርጓል።

ከአባቱ ሕልፈት በኋላ የተናገረውከዚህ በኋላ በእግር ኳስ ተጫዋችነት ብዙ የምቆይ አይመስለኝምሲል የተናገረው ሐሳብ አንደኛው ክፍል አሁን ተዘግቷል። ዘመናዊ እግር ኳስ አንድ ጌጡን እየተነጠቀ ስለመሆኑም ይህ ሌላኛው ምልክት ሆኗል።

የቀረ ጊዜ የለም፤ የተለያየ መልክ ያላቸው ምዕራፎችም ወደ ፍጻሜያቸው እየቀረቡ ነውየሚለው የሊዮኔል ሜሲ የብሔራዊ ቡድን ስንብት አንኳር ነጥብ ነው።

በነዚያ በእግር ኳስ ሜዳ ላይ ባለፉ በኀዘን እና ደስታ፣ በማግኘት እና ማጣት፣ በድል እና ሽንፈት ብሎም በደስታ እና እንባ የታጀቡ ምዕራፎች ውስጥ ትዝታ አለ። ውብ የእግር ኳስ ትዝታ፣ በሰው እና በዘመን መሄድ የማይደበዝዝ ትዝታ!

በእድሪስ አሕመድ

አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: