ባለፉት 2 ወራት ብቻ ከ80 ሺህ ቶን በላይ ቡና ወደ ውጭ በመላክ 546 ሚሊዮን ዶላር ገቢ መገኘቱን የኢትዮጵያ ቡና እና ሻይ ባለሥልጣን ገለጸ።
በ2017 በጀት ዓመት 470 ሺህ ቶን ቡና ወደ ውጭ በመላክ 2.26 ቢሊዮን ዶላር ገቢ መገኘቱን የጠቀሱት የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አዱኛ ደበላ (ዶ/ር)፤ በ2018 በጀት ዓመት 600 ሺህ ቶን ቡና በመላክ 3 ቢሊዮን ዶላር ለማግኘት ታቅዶ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል።
አርሶ አደሩን ተጠቃሚ ለማድረግ በተዘረጋው የአሠራር ሥርዓት ምርቱን በቀጥታ ወደ ተለያዩ ሀገራት መላክ እንዲችል መደረጉ ለገቢው ማደግ አስተዋጽኦ ማድረጉን ነው ዋና ዳይሬክተሩ የተናገሩት።
ከዚህ ቀደም የቡና ጥራት ምርመራ ይደረግ የነበረው በአዲስ አበባ መሆኑን ያነሱት ዋና ዳይሬክተሩ፤ አሁን ግን የጥራት ምርመራው ወደ አርሶ አደሩ እየቀረበ መሆኑን ተናግረዋል።
የቡና ጥራቱን ለማስጠበቅ ወደ አርሶ አደሩ ወርዶ የቡና ቅምሻ ማዕከላትን በማስፋፋት የተሻለ ጥራት ያላቸው የቡና ምርቶችን ወደ ዓለም ገበያ እየተላከ እና የተሻለ ገቢ እየተገኘ እንደሆነም ነው የገለጹት።
በወይንሸት ደጀኔ
#ebcdotstream #ethiopia #coffee #export