የፋይናንስ ደህንነት አገልግሎት ባሰራጨው የጥንቃቄ መልዕክት፥ አንዳንድ በማጭበርበር ድርጊት ላይ የተሰማሩ ሰዎች ከግለሰቦች ፈቃድ ውጪ በሞባይሎቻቸው ውስጥ በመግባት፣ እንደ ዋትስአፕ እና ቴሌግራም የመሳሰሉ የማህበራዊ መገናኛ መተግበሪያዎችን በመጠቀም፣ ግላዊ እና ምስጢራዊ መረጃዎችን በመስረቅ የገንዘብ ማጭበርበር ድርጊት ላይ ተሰማርተው ይገኛሉ ብሏል።
እነዚህ አካላት የግለሰቦችን የማህበራዊ መገናኛ መተግበሪያዎች ከተቆጣጠሩ በኋላ እውነተኛ የአካውንት ባለቤት በመምሰል በግለሰቦቹ ስልኮች ተመዝግበው ለሚገኙ ቤተሰቦች፣ ዘመዶች፣ ጓደኞች እና የሥራ ባልደረቦች እንደተቸገሩ የሚገልፅ የፅሁፍ መልዕክት በመላክ ለዚሁ የማጭበርበር ዓላማ ወደ ተዘጋጀ የባንክ አካውንት እንዲላክላቸው ያደርጋሉ ነው ያለው።
አገልግሎቱ የደረሱትን ጥቆማዎች መሠረት በማድረግ በወንጀል ድርጊቱ ላይ የተሳተፉ አካላትን በመለየት እና በመከታተል በሕግ ተጠያቂ እንዲሆኑ ከሚመለከታቸው ባለ ድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየሠራ መሆኑን ገልጿል።
ኅብረተሰቡ ይህን የማጭበርበር ድርጊት ለመከላከል ወደ ስልኩ ለሚደርሱ መልዕክቶች ምላሽ ከመስጠቱ አስቀድሞ በተለያዩ መንገዶች የመልዕክቱን ትክክለኛነት ደጋግሞ በማረጋገጥ ተገቢውን ጥንቃቄ እንዲያደርግ አሳስቧል።
በተጨማሪም ከሚመለከታቸው ተቋማት የሚተላለፉ የጥንቃቄ መልዕክቶችን በመከታተል ራሱን ከወንጀል ድርጊቶቹ እንዲጠብቅ እና ወንጀል ተፈፅሞ ሲገኝም ለሕግ አስከባሪ አካላት እንዲያሳውቅ መልዕክት አስተላልፏል።
#ebcdotstream #fis #cellphonefraud #mobileappfraud
 
                                                 
                                                                 
                                                                 
                                                                 
                                                                 
                                            