Search

የአውሮፓ ኢንቨስትመንት ባንክ ለሦስተኛው ምዕራፍ የገጠር ፋይናንስ ፕሮግራም የ110 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ ለማድረግ ቃል ገባ

ዓርብ ጥቅምት 07, 2018 106

የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አሕመድ ሽዴ ከዓለም ባንክ እና ከዓለም የገንዘብ ድርጅት ዓመታዊ ስብሰባ ጎን ለጎን ከአውሮፓ ኅብረት ኮሚሽን እና ከአውሮፓ ኢንቨስትመንት ባንክ ከፍተኛ ኃላፊዎች ጋር በዋሽንግተን ዲሲ ተወያይተዋል።
ሚኒስትሩ ከአውሮፓ ኅብረት የዓለም አቀፍ አጋርነት ዳይሬክቶሬት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ማርዬታ ዬገር ጋር ባደረጉት ቆይታ፣ ስትራቴጂካዊ ክልላዊ መሠረተ ልማት ኮሪደሮች ትብብርን ማጠናከር፣ በሂደት ላይ ለሚገኙ የሪፎርም መርሃ-ግብሮች ድጋፍ ማድረግ እና ቅድሚያ በሚሰጣቸው የመንግሥት የትኩረት ጉዳዮች ላይ ያተኮሩ ውይይቶችን አድርገዋል።
ሚኒስቴሩ ከአውሮፓ ኢንቨስትመንት ባንክ የዓለም አቀፍ አጋርነት ዳይሬክተር ቶራያ ትሪኪ ጋር ባደረጉት ውይይት ደግሞ ባንኩ የኢትዮጵያን የልማት አጀንዳዎች በተለይም እንደ አነስተኛ እና መካከለኛ ኢንተርፕራይዝ ፋይናንስ፣ ውኃ፣ ሳኒቴሽን እና ንጽህና እንዲሁም የሴቶች የሥራ ፈጠራ ልማትን ለመሳሰሉ ተግባራት ለሚያደርገው ተሳትፎ እና ድጋፍ አድናቆታቸውን ገልጸዋል።
ቀጣዮቹ የባንኩ የድጋፍ አቅጣጫዎች ለአካታች እና ዘላቂ የገጠር ኢኮኖሚ ልማት ኢኒሼቲቭ እና ለማኑፋክቸሪንግ ሴክተር የፋይናንስ ድጋፍ ማድረግን ጨምሮ ሌሎች ጉዳዮች ላይ እንደሚሆኑም ዘርዝረዋል።
የአውሮፓ ኢንቨስትመንት ባንክ በበኩሉ ለሦስተኛው ምዕራፍ የገጠር ፋይናንስ ፕሮግራም (RUFIP III) የ110 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ ለማድረግ ያለውን ቁርጠኝነት አረጋግጧል።
የገጠር ፋይናንስ ፕሮግራም ለገጠሩ አካባቢ የፋይናንስ ተደራሽነትን ማስፋት፣ የፋይናንስ አሳታፊነትን ማጎልበት እና ሰፊውን የኢትዮጵያ የግብርና ትራንስፎርሜሽን ጥረትን ለመደገፍ ያለመ ነው።
ይህም የኢትዮጵያ መንግሥት እና የአውሮፓ ኅብረት ተቋማት ዘላቂ እና ሁሉን አቀፍ ልማትን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር፣ የግሉ ዘርፍ ዕድገትን ለማጎልበት እና የኢኮኖሚ ትራንስፎርሜሽን ለማፋጠን ያላቸውን አጋርነት የሚያንፀባርቅ ስለመሆኑ ተገልጿል።
 
በዮናስ በድሉ