የገጠር ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ሽግግር ማኅበረሰቡን ከባህላዊ አኗኗር ዘይቤ ወደ ዘመናዊ ኑሮ የሚያሸጋግር ነው ይላሉ የሕግ፣ የሰላም እና የጥናት ተመራማሪና አማካሪው ሮባ ጴጥሮስ (ዶ/ር)።
የገጠር ሽግግር ባህላዊ እሳቤዎችን የመለወጥ አቅም እንዳለው ያነሱት ተመራማሪው፤ የተበታተነውን የገጠር ማኅበረሰብ በማሰባሰብ በዘመናዊ መልክ እንዲኖር ማድረግ የዚህ ሽግግር ዋና ዓላማ እንደሆነም ከኢቲቪ ጋር በነበራቸው ቆይታ አንስተዋል።
የብልጽግና መንግሥት ሰው ተኮር በሆኑ የገጠር ማኅበረሰብ የማዘመን በርካታ ሥራዎች ላይ ትኩረት አድርጎ እየሠራ መሆኑን ሮባ ጴጥሮስ (ዶ/ር) አስረድተዋል።

የመደመር መንግሥት በምግብ ራስን የመቻል ግብ ላይ ለመድረስ በግብርና ዘርፍ ልዩ ትኩረት መስጠቱንም አስታውሰዋል።
ከእጅ ወደ አፍ የሆነውን የግብርና ስርዓት ለመቀየር የገጠሩን አኗኗር ማዘመን መፍትሄ መሆኑን የገለፁት ተመራማሪው፤ የገጠር ሽግግር ለዚህ ስኬት ከሚያበቁ ሥራዎች መካከል አንዱ መሆኑን ጠቁመዋል።
በከተማ ያለው እድገትና አኗኗር በገጠሩ አካባቢም እንዲኖር መሰረተ ልማቶች በስፋት መሥራት እና የገጠሩ ማኅበረሰብ ከቴክኖሎጂ ጋር እንዲላመድ ማድረግም ጠቃሚ መሆኑን ገልፀዋል።
በሜሮን ንብረት