የኢትዮጵያ ሕልውና እና ሁለንተናዊ ብልጽግና ከቀይ ባሕርና ዓባይ ተፋሰስ ልማት ጋር የተሰናሰለ መሆኑን የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ጃፋር በድሩ ገለጹ።
በውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት፣ በመከላከያ ዋር ኮሌጅና በሠመራ ዩኒቨርሲቲ ትብብር "የሁለቱ የውኃ ሥርዓቶችና የኢትዮጵያ ስትራቴጂካዊ ነፃነት፤ የዓባይና የቀይ ባሕር ትስስር እና የአፋር ክልልን ስትራቴጂካዊ ሚና መዳሰስ" በሚል ርዕሰ ጉዳይ በሠመራ ዩኒቨርሲቲ ምክክር እየተካሄደ ይገኛል።
የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ጃፋር በድሩ፥ የምስራቅ አፍሪካ የኃይል ቋት፣ የስልጡን ህዝቦችና አርበኞች ምድር የሆነችው ኢትዮጵያ ከዓባይ ሸለቆና ከቀይ ባሕር ጋር ጥብቅ ቁርኝት ያላትና የአፍሪካ ቀንድ አስኳል መሆኗን ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ የጂኦፖለቲካዊ እሳቤም ከሁለቱ የውኃ አካላት ጋር የሚቃኝ መሆኑን በማንሳት፤ ወደ ቀይ ባሕር ስንቀርብ ኃያልነታችንና እሳቤያችን ይሰፋል ብለዋል።
ላለፉት ሦስት አሥርት ዓመታት ያህል ጂኦፖለቲካዊ በሆነው ስለ ቀይ ባሕርም ሆነ ስለባሕር በር ጉዳይ ምርምርና የፖሊሲ ውይይት ማካሄድ ፈጽሞ የማይታሰብ እንደነበር አስታውሰዋል።
ከሀገራዊ ለውጡ ወዲህ የኢትዮጵያን የቁጭት ዘመን ምላሽ ለመስጠት መንግሥት ስለ ባሕር በር መነጋገር እንደነውር የሚቆጠርበት ዘመን እንዲያከትም ማድረጉን ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ የባሕር በር ጉዳይ ከባሕሩ ባሻገር ከራስ ታሪክ፣ ጂኦግራፊ፣ እውነት፣ ሥነ-ልቦና ጋር መታረቅ ጭምር መሆኑን ተናግረዋል።
የባሕር በር ጥያቄ የቅንጦት ሳይሆን ከራስ ጋር የመታረቅ፣ ራስን የመሆንና መፈለግ፣ ከራስ ታሪክና ማንነት ጋር ዕርቅ የመፈጸም ጉዳይ ነው ብለዋል።
የሠመራ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት መሀመድ ዑስማን (ዶ/ር)፤ መድረኩ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ የሚያስችል ምሁራዊ ውይይት ለማድረግ ወሳኝ ሚና አለው ማለታቸውን ኢዜአ ዘግቧል።
የኢትዮጵያ የቀይ ባሕር በርን የማግኘት ፍላጎትም ከታሪክ፣ ጂኦግራፊና ቀጣናዊ ደኅንነት ጋር በቀጥታ የሚያያዝ ጉዳይ መሆኑን ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ባሕር ኃይል ምክትል አዛዥ ለውጊያ ድጋፍ አገልግሎት ኮሞዶር ተገኝ ለታ በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ብሔራዊ ተጠቃሚነት ከዓባይና ከቀይ ባሕር ጋር በእጅጉ የተቆራኘ ነው ብለዋል።
ከበርካታ ዓመታት በፊት ፈርሶ የነበረውን የኢትዮጵያ ባሕር ኃይል መልሶ በማደራጀት በሰው ኃይል፣ በአደረጃጀት፣ በቴክኖሎጂ አስተማማኝና ጠንካራ ሠራዊት እየተገነባ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
በመድረኩ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ፈትሂ ማህዲ (ዶ/ር)፣ የመንግሥት ከፍተኛ አመራሮች፣የመከላከያ ሠራዊት መኮንኖችና ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል።
#ebc #ebcdotstream #Ethiopia #seaaccess