የሀገራችን የኢኮኖሚ ዋነኛ ምሰሶ የሆነው የግብርና ዘርፍ ለጠቅላላ የሀገር ውስጥ ምርት (GDP) 32 በመቶውን ድርሻ ይይዛል፡፡ ከ79 በመቶ በላይ ለሚሆነው ሕዝብም ዋነኛ የገቢ እና የመተዳደሪያ ምንጭ ነው።
ባለፉት አምስት ዓመታት ተግባራዊ እየተደረገ ባለው ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ አማካኝነት፣ ዘርፉን ከዕለት ጉርስ ፍላጎት ማሟያነት ወደ ዘመናዊ እና ገበያ ተኮር የንግድ እርሻ (ኮሜርሻላይዜሽን) ለማሸጋገር ታላላቅ የሪፎርም እርምጃዎች ተወስደዋል።
ከእነዚህም መካከል የአነስተኛ አምራቾችን ይዞታ ወደ ከፍተኛ ምርታማነት ሥርዓት ማሸጋገር ዋነኛው የትኩረት አቅጣጫ ሆኖ ቆይቷል።
ለዚህ ስኬት መረጋገጥ በግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት የሚመራው የግብርና ኮሜርሻላይዜሽን ክላስተር ፕሮግራም ስትራቴጂካዊ ሚና እየተጫወተ ይገኛል።
መረጃዎች እንደሚያሳዩት ከ2011 እስከ 2017 ዓ.ም የተተገበረው የመጀመሪያው የክላስተር ምዕራፍ ከ4.4 ሚሊዮን በላይ አርሶ አደሮችን ተደራሽ ማድረግ የቻለ ነው፡፡
በክላስተር የታቀፉ አርሶ አደሮችም ከብሔራዊ አማካዩ በ44 በመቶ የላቀ ምርት አስመዝግበዋል።
እንደ ተጨባጭ ማሳያም አማካይ የእህል ምርታማነት መጠን በ86 በመቶ በማደግ በሄክታር 3.18 ቶን ደርሷል።
ይህ ከፍተኛ ምርታማነት አጠቃላይ የግብርና ምርትን በ56 በመቶ እንዲያድግ አድርጎታል፡፡
አርሶ አደሩ ለራሱ ፍጆታ ከተጠቀመ በኋላ ለገበያ የሚያቀርበው የእህል ትርፍ ምርት መጠን በከፍተኛ ሁኔታ እንዲጨምር አድርጓል።
ወደ ሆርቲካልቸር ሰብሎች ስንመጣ በ2015 ዓ.ም ብቻ ወደ ውጭ ከተላኩ ምርቶች ከ658 ሚሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሪ ተገኝቷል።
ይህ ገቢ በ2005 ዓ.ም ከነበረው 245.6 ሚሊዮን ዶላር ጋር ሲነፃፀር የ412.4 ሚሊዮን ዶላር ጭማሪ ያሳየ ነው።
በተለይም በአቮካዶ ምርት ላይ የታየው ስትራቴጂያዊ መሻሻል የወጪ ንግድ መጠኑን በማሳደግ በ2017 ዓ.ም ወደ 5 ሺህ ቶን እና 1.5 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ከፍ አድርጎታል።
ለዚህ ዘመናዊ የግብርና ሽግግር የሎጂስቲክስ መሻሻል ትልቅ አስተዋጽዖ ያበረከተ ሲሆን፣ በአርሶ አደሮች የተመረተውን አቮካዶ በሞጆ ደረቅ ወደብ በማቀዝቀዣ ኮንቴይነር፣ በኢትዮ-ጂቡቲ ምድር ባቡር እና በባሕር ትራንስፖርት ወደ አውሮፓ ገበያ ማቅረብ ተጀምሯል።
የድህረ ምርት ብክነትን ለመቀነስም የኢትዮጵያ መንግሥት ከኔዘርላንድስ መንግሥት ጋር በመተባበር የ27.5 ሚሊዮን ዶላር ኢንቨስትመንት የሚጠይቀውን የማቀዝቀዣ ማዕከል ግንባታን በፍጥነት እያከናወነ ይገኛል።
ይህን ተስፋ ሰጪ የግብርና ኮሜርሻላይዜሽን ስኬት ቀጣይነት ለማረጋገጥ፣ ከ2017 እስከ 2026 ዓ.ም የሚተገበረው አዲሱ ሀገራዊ የሆርቲካልቸር ስትራቴጂ ተቀርጾ ወደ ሥራ ገብቷል።
ስትራቴጂው በቀጣዮቹ ዓመታት የሀገር ውስጥ ፍላጎትን ሙሉ በሙሉ በማሟላት፣ ኢትዮጵያን ከአፍሪካ ቀዳሚ አምራች እና ላኪ እንዲሁም በዓለም ደረጃ ተወዳዳሪ የማድረግ ታላቅ ራዕይ ሰንቋል።
በዚህም የሆርቲካልቸር ምርቶች ከጠቅላላው የግብርና ዓመታዊ ምርት ያላቸውን ድርሻ ከ4.5 ወደ 12 በመቶ፣ ዓመታዊ የውጭ ምንዛሪ ገቢን ወደ 3.3 ቢሊዮን ዶላር እንዲሁም በእሴት ሰንሰለቱ ላይ የሚፈጠረውን ቋሚ የሥራ ዕድል ወደ 2 ሚሊዮን ለማሳደግ ግብ ተቀምጧል።
የተማከለ ዲጂታል የመረጃ ሥርዓት መዘርጋትን ጨምሮ የምርቶችን ደረጃ በመለየት ወደ አውሮፓ እና መካከለኛው ምሥራቅ ገበያዎች የማስፋፋቱ ሥራ የሀገራችንን ተወዳዳሪነት እና የውጭ ምንዛሪ አቅም በእጅጉ የሚያጎለብት ይሆናል።
በለሚ ታደሰ