የኢትዮጵያ የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ አጀንዳ ተጨባጭ እና አዎንታዊ ውጤቶችን እያመጣ መሆኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) አስታወቁ።
ሚኒስትሩ በለንደን በተካሄደው የዩኬ-ኢትዮጵያ የንግድ እና ኢንቨስትመንት ፎረም ላይ እንደገለጹት፣ ማሻሻያው በገበያ የሚወሰን የውጭ ምንዛሬ ተመን፣ የዘመነ የገንዘብ ፖሊሲ፣ የግብር አስተዳደር ጥንካሬ እና በዋና ዋና የኢኮኖሚ ዘርፎች ላይ የግል ዘርፉን ተሳትፎ ማሳደግ ላይ ትኩረት ያደረገ ነው።
በማሻሻያው የተመዘገቡ ዋና ዋና ስኬቶች፡-
• የሀገር ውስጥ ገቢ - በ61 በመቶ ዕድገት ያሳየ ሲሆን፣ የግብር ከሀገር ውስጥ ጠቅላላ ምርት (GDP) ጥሬታም ከ6.2 በመቶ ወደ 7.8 በመቶ አድጓል።
• የዋጋ ግሽበት - ከነበረበት 16 በመቶ ወደ 10.9 በመቶ ዝቅ እንዲል ተደርጓል።
• የሸቀጦች ኤክስፖርት - የ119 በመቶ ከፍተኛ ዕድገት አስመዝግቧል።
• የውጭ ምንዛሬ አቅርቦት - ቀደም ሲል የባለሀብቶች ዋነኛ ስጋት የነበረው የውጭ ምንዛሬ እጥረት አሁን ላይ ተቀርፎ አቅረቦቱ እና ክምችቱ መሻሻል ያሳየ ሲሆን፣ የባለሀብቶች መተማመንም በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ ይገኛል።
ሚኒስትሩ አክለውም የዓለም አቀፍ የገንዘብ ድርጅት (IMF) ለኢትዮጵያ በዚህ ዓመት የ9.2 በመቶ ዕድገት መተንበዩን፣ የሀገር ውስጥ ትንበያ ደግሞ የ10.2 በመቶ ዕድገት እንደሚያሳይ ጠቁመዋል።
ይህም ኢትዮጵያን በቀጣይ ዐሥርተ ዓመታት በአፍሪካ ግንባር ቀደም ኢኮኖሚ ለማድረግ የተያዘውን ራዕይ ለማሳካት መሠረት የሚጥል ነው።