የማርበርግ ቫይረስን ለመመርመር የሚያስችል ተንቀሳቃሽ ወይም የሞባይል ላብራቶሪ በሽታው ወደ ተከሰተበት ስፍራ እየተጓጓዘ መሆኑን የጤና ሚኒስትር ዶ/ር መቅደስ ዳባ ገለፁ፡፡
በኢትዮጵያ በተከሰተው የማርበርግ ቫይረስ ወረርሽኝ ዙሪያ የጤና ሚኒስቴር እና የህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት በጋራ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል።
መግለጫውን የሰጡት ዶ/ር መቅደስ ዳባ፤ በሽታው በተከሰተባቸው አካባቢዎች የለይቶ ማቆያ ቦታዎችን ከማዘጋጀት ጀምሮ የህክምና ቁሳቁስና ግብዓት የማሟላት ስራ መሰራቱን ተናግረዋል፡፡
ከቫይረሱ ጋር ንክኪ ያላቸው ሰዎችን በመለየትም ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር የማርበርግ ቫይረስን በአጭር ጊዜ ለመቆጣጠር በቅንጅት እየተሰራ እንደሚገኝ ሚኒስትሯ ገልፀዋል፡፡
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጂንካ ከተማ ወረርሽኙ መከሰቱ ከተረጋገጠ በኋላ የ17 ሰዎች የላብራቶሪ ናሙና ተወስዶ መመርመሩን እና 3 ሰዎች በሽታው እንደተገኘባቸውም ተናግረዋል።
እነዚህን 3 ሰዎች ጨምሮ እስካሁን 6 ሰዎች ህይወታቸው ያለፈ መሆኑን የገለፁት ሚኒስትሯ፤ 3 ሰዎች በጥርጣሬ ደረጃ፣ 3 ሰዎች ደግሞ በክሊኒካል ላብራቶሪ የተረጋገጠ መሆን አስረድተዋል።
የጤና ሚኒስቴር ወረርሽኙ ከተለየ በኋላ ንክኪ ያላቸው ሰዎችን ከመለየት ጀምሮ የተለያዩ ስራዎች እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።
በዛሬው ዕለትም ወደ ጂንካ የሞባይል ላብራቶሪ ጉዞ መጀመሩን ዶ/ር መቅደስ ተናግረዋል።
በየወረዳው የተቋቋሙ የድንገተኛ ምላሽ ሰጪ ማዕከላት ስራ እንዲጀምሩ መደረጉን ገልጸዋል።
በንክኪ የሚተላለፍ በሽታ በመሆኑ በተለይ ምልክት ካሳዩ ሰዎች ጋር ንክኪን መቀነስ፣ እጅን በሳሙና መታጠብና ሳኒታይዘር መጠቀም ያስፈልጋል ብለዋል።
በሽታው በተከሰተባቸው አካባቢዎች የለይቶ ማቆያ ቦታዎችን ከማዘጋጀት ጀምሮ የህክምና ቁሳቁስና ግብዓት ማሟላት ስራ መሰራቱን ዶ/ር መቅደስ ጠቁመዋል።
በሽታው እስካሁን የተረጋገጠ መድሀኒት የለውም ያሉት ሚንስትሯ፤ መከላከል ላይ ትኩረት አድርገን እንሰራለን ብለዋል።
በበሽታው ተጠርጥረው ህይወታቸው ያለፉ ሰዎች የቀብር ስርዓት ጤና ሚንስቴር እና የኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት በሚያወጣቸው መመሪያዎች መሠረት ሊደረግ እንደሚገባ አሳስበዋል።
የማርበርግ ቫይረስ የተለያዩ የአፍሪካ ሀገራትን ጨምሮ በ12 ሀገሮች እንደታየ መረጃዎች የሚጠቁሙ ሲሆን፤ እ.አ.አ በ1967 በጀርመን ሀገር ማርበርግ ከተማ መጀመሪያ መከሰቱን ተከትሎ ስያሜውን ማግኘቱ ይገለፃል።
በሞላ ዓለማየሁ