በሀዋሳ ልዩ የኢኮኖሚ ዞን ውስጥ ከሚገኙ አንዱ የሆነው ቶዮ ሶላር አምራች ኩባንያ በሀዋሳ ከተማ አስተዳደር፣ ቱላ ክፍለ ከተማ፣ ጨፌ ቆምቦኦ ትምህርት ቤት በመገኘት አቅም ለሌላቸው ተማሪዎች ከ5 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመት የተለያዩ የትምህርት ቁሳቁስ ድጋፍ አድርጓል።

የሀዋሳ ልዩ የኢኮኖሚ ዞን ዋና ኃላፊ አቶ ማቴዎስ አሸናፊ በመርሐ ግብሩ ላይ፥ ድርጅቱ አቅም ለሌላቸው ተማሪዎች ያደረገው ድጋፍ ለመማር ማስተማር ሥራ ስኬታማነት ትልቅ ትርጉም ያለው ነው ብለዋል።
የቶዮ ሶላር አምራች ኩባንያ ተወካይ በበኩላቸው፥ ድርጅቱ የሶላር ምርት በማምረት ለሀገሪቱ ኢኮኖሚ አስተዋጽኦ ከማድረግ በተጨማሪ ለብዙ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠሩን ገልጸዋል።

አክለውም፥ ኩባንያው ድጋፉን ያደረገው የነገ የሀገር ተረካቢዎች የሆኑትን አዳጊዎች በማብቃት የድርሻውን ኃላፊነት ለመወጣት ነው ማለታቸውን የሲዳማ ክልል ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ያደረሰን መረጃ ያመለክታል።
#ebcdotstream #toyosolar #hawassa #communityservice