ከተለያዩ ግለሰቦች በተለያዩ ጊዜያት የጠፉና የተሰረቁ ሞባይል ስልኮችን የቴሌግራም አካውንቶች የይለፍ ቃሎችን በመጥለፍ የግል ተበዳዮች ወደሚያውቋቸው ሰዎች “ቸግሮኛል፣ ቤተሰብ ታሞብኛል፣ ገንዘብ አበድሩኝ” የሚሉ መልዕክቶችን በመላክ የማታለል ወንጀሎችን ሲፈፅሙ የነበሩ ግለሰቦች ላይ ተገቢው ጥናትና ክትትል ሲደረግ መቆየቱን ፖሊስ አስታውቋል።
በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ የመሳለሚያ አካባቢ ፖሊስ ጣቢያም ይህን የወንጀል ድርጊት ይፈፅማሉ በሚል በጠረጠራቸው ግለሰቦችና አካባቢዎች ላይ በተደረገ ጥናትና ክትትል ሙዲ ሁሴን የተባለን ተጠርጣሪ በጥር 26 ቀን 2018 ዓ.ም ከቀኑ 10፡00 ሰዓት ላይ በክፍለ ከተማው ወረዳ 8 ልዩ ቦታው አብዶ በረንዳ አካባቢ በቁጥጥር ስር ሊያውለው ችሏል።
ፖሊስ ተጠርጣሪውን በቁጥጥር ስር ካዋለ በኋላም በእጁ ላይ በተገኙት ሁለት ተንቀሳቃሽ ስልኮቹ ላይ ባደረገው ማጣራት 20 ገንዘብ የተላለፉባቸው የተለያዩ ባንኮች አካውንት ቁጥሮች ከመገኘታቸውም በላይ 72 ሲም ካርዶች በቁጥጥር ስር ውለዋል።
ፖሊስ የምርመራ ስራውን በማስፋት በተጨማሪ አባስ አብዱና አሊ ሳኖ ኑሪ የተባሉ ተጠርጣሪዎችን የሰሌዳ ቁጥር ኮድ 2-B85392 አ/አ ከሆነ ራቫ4 ተሽከርካሪ ጋር በቁጥጥር ስር ሲያውል፣ 6 ተንቀሳቃሽ ስልኮችና 7 ሲም ካርዶች ተይዘዋል።
በቁጥጥር ስር ከዋሉት ሦስት ተጠርጣሪዎች በአጠቃላይ 79 ሲም ካርዶች፣ 8 ተንቀሳቃሽ ስልኮችና 1 ተሸከርካሪ በቁጥጥር ስር ውለዋል።
ተመሳሳይ የወንጀል ድርጊት ተፈጽሞብኛል የሚል ግለሰብ በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ በመቅረብ መረጃ መስጠት እንደሚችል ፖሊስ አስታውቋል።
ግለሰቦች ከሚያውቁት የስልክ ጥሪ የእርዳታም ይሁን ሌሎች መልዕክቶች ሲደርሳቸው የመልዕክት ላኪውን ማንነት ማረጋገጥ እንደሚጠበቅባቸው የአዲስ አበባ ፖሊስ ጠቅላይ መምሪያ መልዕክት አስተላልፏል።
#Ethiopia #AddisAbaba #Police #EthiopianBroadcastingCorporation