Search

የአፍሪካ መዲናነት መሠረት - የኢትዮጵያ ብርቱ ዲፕሎማሲያዊ ጉዞ

ማክሰኞ የካቲት 03, 2018 108

ኢትዮጵያ በታሪኳ ጠንካራ የሁለትዮሽ እና የባለብዙ ወገን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ያላት ሀገር መሆኗ ይታወቃል።

ይህ የታሪክ አሻራ በተለይም የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (ECA) መቀመጫውን አዲስ አበባ እንዲያደርግ በማስቻል ረገድ የላቀ ሚና ተጫውቷል።

ኢትዮጵያ የመጀመሪያውን የአፍሪካ ጉባኤ ማስተናገድ የቻለችው በታሪካዊ ነጻነቷ እና በነበራት የዲፕሎማሲ ተሰሚነት ነው።

... 1958 የተመሰረተው የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን መቀመጫውን አዲስ አበባ እንዲያደርግ የተወሰነው በወቅቱ በነበረው ብርቱ ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ነው።

በወቅቱ የሥራና መገናኛ ሚኒስትር የነበሩት ልዑል ራስ መንገሻ ስዩም እንደሚገልጹት፤ የኮሚሽኑ መቀመጫ አዲስ አበባ መሆኑ ለመዲናዋ ዘመናዊ የከተሜነት ታሪክ እና ለግዙፍ መሰረተ ልማቶች ግንባታ ዋነኛ መነሻ ሆኗል።

የአፍሪካ አዳራሽ (Africa Hall) ከመገንባቱ በፊት ስብሰባዎች የሚካሄዱት በወቅቱ በነበሩት የመከላከያ ሚኒስቴር እና የንግድ ሥራ ኮሌጅ አዳራሾች ውስጥ ነበር።

ይሁን እንጂ አህጉራዊ ውይይቶችን በከፍተኛ ደረጃ ለማካሄድ ዘመናዊ አዳራሽ መገንባት የግድ አስፈላጊ በመሆኑ የአሁኑ የአፍሪካ አዳራሽ ግንባታ ተጀመረ።

ይህ ፍላጎትም ለቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ እና ከመሃል ከተማ ወደ አውሮፕላን ማረፊያው ለሚወስደው ዘመናዊ መንገድ መሰራት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ነበረው።

ለህንጻው ግንባታ በወቅቱ አምስት ሚሊዮን ብር እና ሦስት ዓመታት ጊዜ እንደሚፈጅ ተገምቶ የነበረ ቢሆንም፤ ግንባታው በአንድ ዓመት ውስጥ መጠናቀቅ እንዳለበት በመወሰኑ "ባርኔሮ" የተባለ የውጭ ተቋራጭ ሥራውን ተረክቦታል።

በሦስት ዓመት የሚጠናቀቀውን ፕሮጀክት በአንድ ዓመት ለማጠናቀቅ ሰራተኞች 24 ሰዓታት ያለምንም ማቋረጥ እንዲሰሩ ተደርጓል።

ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ለፕሮጀክቱ ልዩ ትኩረት በመስጠት፣ በእኩለ ሌሊት ሳይቀር በቦታው ተገኝተው የሥራውን ሂደት ይከታተሉ ነበር።

ይህ ጥረት ፍሬ አፍርቶ ... 1963 የአፍሪካ መሪዎች የአፍሪካ አንድነት ድርጅት (OAU) መመስረቻ ቻርተርን በዚሁ ታሪካዊ አዳራሽ ውስጥ ለመፈረም በቅተዋል።

ዛሬም ኢትዮጵያ ይህንን ታሪካዊ ሚናዋን በማስቀጠል በርካታ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ሁነቶችን በብቃት ማስተናገዷን ቀጥላለች።

ንፍታሌም እንግዳወርቅ