Search

የሰው ሰራሽ አስተውሎት አብዮት ለኢነርጂ ዘመናዊነትና ለቀጣናዊ የኢኮኖሚ ትስስር

እሑድ ግንቦት 02, 2018 45

የሰው ሰራሽ አስተውሎት (ኤ አይ) የዓለምን የኢነርጂ አቅርቦት ሥርዓት ከመቀየር ባለፈ ሀገራትን በኢኮኖሚ የማስተሳሰር ግዙፍ አቅም እንዳለው የሚጠቁም ዓለም አቀፍ ጥናታዊ ትንታኔ በዱባዩ የዓለም መንግሥታት ጉባኤ ላይ ይፋ ተደርጓል።
ይህ ጥናት እስከ ፈረንጆቹ 2032 ድረስ ባለው ጊዜ ውስጥ ቴክኖሎጂው በጂኦ-ፖለቲካዊ መረጋጋት እና በዘላቂ ልማት ላይ የሚኖረውን አዎንታዊ ሚና በዝርዝር ያሳያል።
በተለይ "የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ዕድል ክላስተሮች" የሚባሉ አዳዲስ የልማት ቀጣናዎች መፈጠር ለኢኮኖሚ መነቃቃት ቁልፍ ሚና እንደሚጫወቱ ተመላክቷል።
እነዚህ ክላስተሮች የዳታ ማዕከላትን፣ የጥናት ተቋማትን እና የታዳሽ ኃይል መሠረተ ልማቶችን በአንድ ማዕቀፍ በማገናኘት አዳዲስ ዕድሎችን ይፈጥራሉ።
ይህም እንደ ቻይና እና ሕንድ ያሉ ሀገራት የፖለቲካ ልዩነቶቻቸውን ወደ ጎን በመተው በቴክኖሎጂ እና በኃይል ልማት ላይ በጋራ እንዲሰሩ በር የሚከፍት ወሳኝ እርምጃ ነው።
በተጨማሪም ቴክኖሎጂው በኃይል ሥርዓቶች ላይ ሊያጋጥሙ የሚችሉ የሳይበር ስጋቶችን ለመቋቋም መረጃን በተለያዩ ቦታዎች በማሰራጨት አስተማማኝ ጥበቃ ማድረግ የሚያስችል ሲሆን፣ የሉዓላዊ ሀብት ፈንዶችም ዝቅተኛ የካርቦን ልቀት ላላቸው ፕሮጀክቶች ፋይናንስ በማቅረብ ለአየር ንብረት ጥበቃ ትልቅ ተስፋ እየሰጡ ይገኛል።
በተለይ ወጣት የሰው ኃይል ባላቸው አዳጊ ሀገራት የክህሎት ሥልጠናን ማስፋፋት ለኢኮኖሚ ዕድገት ብቻ ሳይሆን ለቀጠናዊ ሰላምና ሀብትን በብቃት ለማስተዳደር ወሳኝ መሆኑ ተረጋግጧል።
ባጠቃላይ የሰው ሰራሽ አስተውሎትን ከኃይል አቅርቦት እና ከዲፕሎማሲ ጋር አጣጥሞ መምራት ከተቻለ፣ ለሰው ልጅ የላቀ የብልጽግና ዘመንን እንደሚያመጣ ጥናቱ ያመላክታል።
በቀጣይ የሚካሄዱ እንደ "ዓለም አቀፍ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ጉባኤ በአፍሪካ" ያሉ መድረኮችም ይህንን የቴክኖሎጂ አቅም ለሁሉም ተደራሽ ለማድረግ ጉልህ ሚና ይጫወታሉ።
በመሐመድ ፊጣሞ