ቀደም ሲል በውጭ ኩባንያዎች ተሳትፎ ሊሳካ ያልቻለውን ታላቁን የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት፣ ኢትዮጵያውያን ወጣቶችና ባለሙያዎች በሚያስደንቅ ብቃት ማጠናቀቃቸውን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ።
ፕሮጀክቱ የአካባቢውን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ፤ ለከተማዋ ነዋሪዎች ትልቅ የምሥራች ይዞ የመጣ መሆኑንም ጠቁመዋል።

ቀደም ሲል በወንዙ ዳርቻ ይገኙ የነበሩና ያለ ፕላን የተጨናነቁ መኖሪያ ቤቶች ለክረምት ጎርፍ አደጋ የተጋለጡ፣ የመኪና መግቢያ መንገድ የሌላቸውና ለነዋሪዎች ምቾት የማይሰጡ እንደነበሩ ጠቅላይ ሚኒስትሩ አስታውሰዋል።

በአሁኑ ወቅት ግን ይህንን አስቸጋሪ እውነታ ሙሉ በሙሉ የሚቀይር፣ የሕዝቡን የኑሮ ዘይቤ የሚያሻሽልና ለእንቅስቃሴ ምቹ የሆነ ማራኪ አካባቢ መፈጠሩን አስረድተዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ አክለውም፤ “ይህ ሰፊ የልማት ሥራ ከአካባቢና አፈር ጥበቃ፣ ውኃን በንጽሕና ከመያዝና ለዕይታ ማራኪ ከመሆን አንጻር በማንኛውም መመዘኛ እጅግ የሚያኮራ ነው፤ ከዚህም በላይ ለሌሎች የአፍሪካ አገራት ትልቅ ትምህርት የሚሰጥ ነው” ብለዋል።
የፕሮጀክቱ ወቅታዊ ደረጃና የቀጣይ ሥራዎች፦
በአሁኑ ወቅት ከእንጦጦ ተነስቶ እስከ ቦሌ ያለው የፕሮጀክቱ ክፍል በአብዛኛው የተጠናቀቀ ሲሆን፤ በቀጣዮቹ ሁለትና ሦስት ወራት ውስጥ እስከ ፒኮክ ያለው ቀሪ አካል ሙሉ በሙሉ ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት እንደሚሆን ታውቋል።
በቀጣይም ውኃውን ይበልጥ የማጥራትና ወደ መጠጥ ደረጃ የማሸጋገር ተጨማሪ ሥራዎች እንደሚከናወኑ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጠቁመዋል።
የእግር ጉዞ ጥሪ፦
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ለአዲስ አበባ ነዋሪዎችና ለጎብኚዎች ባስተላለፉት መልእክት፤ ኅብረተሰቡ በሳምንት አንድ ወይም ሁለት ቀን ጠዋት ጠዋት ከእንጦጦ በመነሳት እስከ ቀጨኔና ፒያሳ ያለውን ከ10 እስከ 15 ኪሎ ሜትር የፓርክ መንገድ በእግር እንዲጓዙ ጋብዘዋል።
መንገዱ በቀዝቃዛ አየርና በማራኪ እይታ የታጀበ በመሆኑ፤ ሳይደክሙ አካልን ለመገንባትና የአገርን ውበት በአካል ተገኝቶ ለማድነቅ ልዩ ዕድል እንደሚፈጥርም ገልጸዋል።
በመሐመድ ፊጣሞ