የአሠራር መዘግየትና ቢሮክራሲ ቀርቶ ነገሮች ሁሉ በቴክኖሎጂ የሚፈጥኑበት አዲስ ምዕራፍ ላይ እንገኛለን።
በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የዲጂታል አማካሪ ማርያም ሰይድ እንዳሉት፣ የዲጂታል ሥርዓቶች የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ የኢኮኖሚ ሽግግር በማስተሳሰር የለውጥ ሂደቱን በከፍተኛ ፍጥነት እያፋጠኑት ይገኛሉ።
አሁን ላይ ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን በሀገራችን መዋቅራዊ ለውጦችን፣ ገበያዎችንና ተቋማትን በማገናኘት ምርታማነትን ለማሳደግ ዋነኛ መሣሪያ እየሆነ መጥቷል።
ይህ የዲጂታል ሥርዓት የኢኮኖሚ እንቅስቃሴያችንን ሙሉ በሙሉ እየቀየረባቸው ያሉ አራት ዋና ዋና መንገዶች አሉ። እነሱም የመረጃ አለመመጣጠንን መቀነስ፣ የገበያ ተሳትፎን ማስፋፋት፣ ግብይቶችንና የአገልግሎት አሰጣጥን ማፋጠን እንዲሁም በተቋማት መካከል ያለውን የሥራ ትስስር ማሻሻል ናቸው።
ለዚህ ትልቅ ጉዞ ደግሞ የዲጂታል መሠረተ ልማቱ እንደ ማዕከል እያገለገለ ሲሆን፣ በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀሱ ስኬቶችም ተመዝግበዋል።
የ“ፋይዳ” ዲጂታል መታወቂያ እስካሁን ከ45 ሚሊዮን በላይ ዜጎችን በመመዝገብ በኢኮኖሚው ውስጥ የታማኝነትና የተደራሽነት መሠረት ጥሏል። በፋይናንስ ዘርፉም ቢሆን ባለፉት ዘጠኝ ወራት ብቻ ከ24 ትሪሊዮን ብር በላይ ግብይት በዲጂታል ክፍያ ሥርዓት መፈጸሙ የገንዘብ ዝውውር ፍጥነትንና የፋይናንስ አካታችነትን በሚያስደንቅ ሁኔታ አሳድጎታል።
በተመሳሳይ 217 የመንግሥት ተቋማትን ያስተሳሰረው የ“መሰቦ” ሥርዓት ከ1 ሺህ 600 በላይ አገልግሎቶችን በአንድ መድረክ በማቅረብ ቀድሞ የነበረውን የተበታተነ አሠራር ሙሉ በሙሉ ቀይሮታል። ይህ የዲጂታል ሽግግር ዘላቂ እንዲሆንም በኢነርጂ አቅርቦትና በሰው ኃይል ልማት ላይ ትልቅ ትኩረት ተሰጥቷል።
ሀገራችን 98 በመቶ ታዳሽ በሆነ የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት የላቀ የማምረቻ ኢንዱስትሪዎችን ለማንቀሳቀስ መሠረት የጣለች ሲሆን ይህም በዓለም አቀፍ የቴክኖሎጂ ምርትና የእሴት ሰንሰለት ውስጥ እንድትሳተፍ ዕድል እየፈጠረላት ነው።
በተጨማሪም የ“5 ሚሊዮን ኮደሮች” ኢኒሼቲቭ ዜጎች ቴክኖሎጂን በምርታማ መንገድ እንዲጠቀሙና የሰው ሠራሽ አስተውሎት (AI) አቅምን እንዲገነቡ በማድረግ ለኢኮኖሚ ሽግግሩ አስፈላጊውን የሰው ኃይል እያዘጋጀ ይገኛል።
ዲጂታል ሥርዓቶች መንግሥት ሀገርን የሚመራበትን መንገድ ጭምር እየቀየሩት ሲሆን፣ ይህም የታክስ መሠረትን ለማስፋትና መረጃን መሠረት ያደረገ ፈጣን ውሳኔ ለመስጠት እንደሚያስችል አማካሪዋ ማርያም ሰይድ አስታውቀዋል።
መጪው ጊዜ የቴክኖሎጂ ባለቤት የሆኑት ሳይሆን ቴክኖሎጂን በልማት ጉዟቸው ውስጥ በብቃት ማቀናጀትና ማስተሳሰር የቻሉ አገራት በመሆኑ፣ ኢትዮጵያም ይህንን የተቀናጀ የዲጂታል ሥነ-ህንፃ የመገንባት መንገድ መርጣ በለውጥ ጎዳና ላይ ትገሰግሳለች።
በላሉ ኢታላ