ለሀገራዊ ምክክር ጉባኤ በተገኙበት የወለዱት ሁለቱም አራስ እናቶች ጉባኤውን አጠናቅቀው ወደ መጡበት እስኪመለሱ ድረስ የሚያስፈልጋቸውን ድጋፍ እናደርግላቸዋለን ሲሉ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ።
ከንቲባዋ በማኅበራዊ ትስስር ገፃቸው ባስተላለፉት መልዕክት፣ ሃዳ አልማህዲ ከቤኒሻንጉል ጉምዝ ክልል ለሀገራዊ ምክክር ከተፎካካሪ ፓርቲ ተወክላ የተጣለባትን ውክላና እና ኃላፊነት በታላቅ የሀገር ፍቅር እና የእኔነት ስሜት እየተወጣች እያለ ወንድ ልጅ በሰላም ተገላግላለች ብለዋል።
እኛም ወ/ሮ ሃዳን በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ማረፊያ ክፍል አዘጋጅተን ለአራስ የሚያስፈልጉ ቁሳቁሶችን አሟልተን እንኳን ደስ አለሽ ብለን ጠይቀናታል ነው ያሉት።
ወ/ሮ ሃዳ አልማህዲ በታሪካዊው ሀገራዊ ምክክር ወቅት ላይ የወለደችውን ወንድ ልጅ ኮሚሽን ብላ ስም ማውጣታቸውንም አስታውሰዋል።
ወጣቷ የመጣችበትን ታላቅ ሀገራዊ ዓላማ ለማሳካት ከጥቂት ቀናት እረፍት በኋላ ወደ ሀገራዊ ምክክር ጉባኤው እንደምትመለስ መናገሯንም ጠቁመዋል።
ለሀገራዊ ምክክር ጉባኤ በተገኙበት የወለዱት ሁለቱም አራስ እናቶች የመጡበትን ሀገራዊ ምክክር ጉባኤ ያለምንም ችግር አሳክተው እንዲመለሱ ለምክክሩ በቅርበት በሚመቻቸው ቦታ ማረፊያ አዘጋጅተንላቸዋል ሲሉም ከንቲባዋ ገልጸዋል።
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: