የትምህርት ሚኒስቴር አመራሮች እና ሠራተኞች በ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸም እና በቀጣይ ዓመት እቅድ ላይ ውይይት አድርገዋል።
የትምህርት ሚኒስትሩ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፣ ትምህርት የሀገር ዕድገትም ሆነ ውድቀት ነጸብራቅ በመሆኑ በትኩረት ሊሠራበት ይገባል።
ባለፉት 5 ዓመታት ለትምህርት ጥራት መሠረት የሚጥሉ ቁልፍና አበይት ተግባራት መከናወናቸውን ተናግረዋል።
ከተከናወኑ ውጤታማ ሥራዎች መካከልም የሥርዓተ ትምህርት ለውጥና የትምህርት ቤቶችን መሠረተ ልማት ማሻሻል በተለይም ደረጃቸውን የጠበቁ የቅድመ አንደኛ፣ አንደኛ እና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ግንባታና እድሳት ሥራ እንደሚገኙበት ገልጸዋል።
የወደፊቱ መሪዎችና ሳይንቲስቶች የሚፈሩባቸው ልዩ አዳሪ ትምህርት ቤቶች በሁሉም ክልሎች የመገንባት እና የማቋቋም ሥራ እየተሠራ መሆኑን ፕሮፌሰር ብርሃኑ አመላክተዋል።
የሁለተኛ ደረጃ መጻሕፍትን 1 ለ 1 ከማዳረስ በተጨማሪ ክልሎችን በመደገፍ የቅድመ አንደኛና አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶችን የመማሪያ መጽሐፍ በማሳተም ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን ጠቁመዋል።
ባለፉት አምስት ዓመታት በተሠራው ሥራ በትምህርት ቤት የተማሪዎች ምገባ አቅም 8.9 ሚሊዮን ማድረስ መቻሉን ገልጸው፣ በቀጣይ በትኩረት ሊሠራ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
በ12ኛ ክፍል ፈተና ከኩረጃና ከስርቆት ነጻ እንዲሆን በ2016 የተጀመረውን የበይነ መረብ ፈተና በዚህ ዓመት ከ62 በመቶ በላይ ማድረስ መቻሉንና በቀጣይ ዓመት 100 ፐርሰንት ለማድረስ እየተሠራ መሆኑን ጠቁመዋል።
በከፍተኛ ትምህርት ረገድም የዩኒቨርሲቲ አስተዳደር ቦርድና አመራሮች ከአካባቢያዊነት ነጻ በሆነ መንገድ በብቃትና በውድድር ላይ የተመሠረተ አኳኋን እንዲመረጡና እንዲመደቡ የሚያስችል ሥርዓት ተፈጥሮ ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን አስረድተዋል።
ከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን በተልዕኮና ባላቸው ጸጋ መሠረት የመማር ማስተማር ምርምር እና የማኅበረሰብ አገልግሎት ሥራዎችን እንዲሰጡ ሥርዓት ተበጅቶ ተግባራዊ መደረጉን ማብራራታቸውን የሚኒስቴሩ መረጃ አመላክቷል።
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: