ኢትዮጵያ በ2011 ዓ.ም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃግብርን ሀ ብላ ስትጀምር ዓላማዋ አካባቢን መጠበቅ ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያን ታሪክ እና የዜጎችን አስተሳሰብ የመለወጥ ትልቅ ራዕይ ነበረው።
በ2011 ዓ.ም በየዓመቱ ከሚተከለው በርካታ ቢሊዮን ችግኞች በተጨማሪ "በአንድ ሰው 40 ችግኝ" እንዲሁም "በአንድ ጀምበር 200 ሚሊዮን ችግኝ" ለመትከል እቅድ ተይዞ ወደ ተግባር ሲገባ በርካቶች "ይህ አይሆንም፣ ቅዥት ነው" በማለት ተስፋ ለማስቆረጥ ጥረት አድርገው ነበር።
ሆኖም ኢትዮጵያውያን በነቃ ሕዝባዊ ንቅናቄ እና በተግባር በሰጡት ምላሽ በአንድ ጀምበር ዘመቻ ታቅዶ የነበረውን 200 ሚሊዮን አልፎ ሐምሌ 22 ቀን 2011 ዓ.ም በመላ ኢትዮጵያ 353 ሚሊዮን 633 ሺህ 660 ችግኞችን መትከል ተችሏል፡፡
ከ2011 እስከ 2018 ዓ.ም የተመዘገበው የጽናት እና የተስፋ ጉዞ ከስድስት ዓመታት በፊት የተዘራው የችግኝ ተከላ ዘመቻ ዛሬ ላይ ከዘመቻ ሥራ ወጥቶ የመላው ኢትዮጵያዊ ባህል እና መለያ መሆን ችሏል።
አይሆንም ላሉት አካላት በየዓመቱ በሥራ እና በውጤት እየመለሰች የመጣችው ኢትዮጵያ፣ በ2018 ዓ.ም "ተስፋን እንትከል " በሚል ታላቅ ሀገራዊ መሪ ቃል ሂደቱን በይፋ ጀምራለች።
ይህ ከ2011 ዓ.ም በአንድ ጀምበር ከ200 ሚሊዮን ዕቅድ የተነሳው ንቅናቄ ዛሬ በአንድ ጀምበር ወደ 800 ሚሊዮን ማደጉ በሀገራችን በየዓመቱ እያደገ የመጣውን አቅም በግልጽ ያሳያል።
የ2011 ዓ.ም ጅማሮ ትልቁ ስኬት "አይቻልም" የሚለውን የጠላት እና የተስፋ አስቆራጮችን ትርክት በመስበር በኅብረት ከተነሳን ማሳካት እንችላለን የሚል ፅኑ ሀገራዊ እምነት መፍጠሩ ነው።
በ2011 ዓ.ም የተጀመረው ሥራ አፈር ከመሸርሸር እና ከደን ጭፍጨፋ መከላከል ቢሆንም በ2018 ዓ.ም ግን እንደ ማካዴሚያ፣ ኮኮናት፣ ቡና እና የፍራፍሬ ተክሎችን በስፋት በማካተት የኢትዮጵያን የውጭ ምንዛሬ ገቢ የሚያሳድግ እና የምግብ ዋስትናን የሚያረጋግጥ ዘመናዊ የልማት ምሰሶ ሆኗል።
"ተስፋን እንትከል" የሚለው የዘንድሮው መሪ ቃል በፈተናዎች ውስጥ ያለችውን ሀገር በኅብረት እና በአረንጓዴ ልማት እርስ በእርስ በማስተሳሰር ለቀጣዩ ትውልድ የተረጋጋች እና የበለፀገች ኢትዮጵያን ለማስረከብ ያለውን ጽኑ ፍላጎት ያመላክታል።
በ2011 ዓ.ም በ353 ሚሊዮን በላይ የአንድ ጀምበር ተከላ የተጀመረው የተስፋ ጉዞ ዛሬ በ2018 ዓ.ም በ800 ሚሊዮን አዲስ የታሪክ ምዕራፍ ሊጽፍ ዝግጅቱን ጨርሷል።
ኢትዮጵያ ለሚነሱባት ጥርጣሬዎች በተግባር እየመለሰች የተተከሉ ችግኞች አድገው ፍሬ ማፍራት እንደጀመሩት ሁሉ የዕድገት እና የሰላሟ ተስፋም ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ ይሄዳል።
በሃና ምንዳሁን
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: