Search

የቀድሞ የማዕድን ሚኒስትር እና አንጋፋዋ ዲፕሎማት አምባሳደር ስንቅነሽ እጅጉ ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ

ዓርብ ሐምሌ 24, 2018 187

በኢትዮጵያ በሳይንስ፣ በመንግሥት አስተዳደር እና በዲፕሎማሲው ዘርፍ የላቀ ስኬት በማስመዝገብ ለሀገራቸው ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያበረከቱት አምባሳደር ስንቅነሽ እጅጉ ባደረባቸው ሕመም በሕክምና ሲረዱ ቆይተው 69 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም ተለይተዋል።

የአምባሳደር ስንቅነሽ እጅጉ የትምህርት እና የሥራ ሕይወት ታሪክ በአጭሩ

በመጋቢት ወር 1948 . በምዕራብ ሸዋ ዞን አምቦ ከተማ የተወለዱት አምባሳደር ስንቅነሽ፤ በልጅነት ዘመናቸው በተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች ተዘዋውረው ትምህርታቸውን ተከታትለዋል።

የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን 1972 . በኬሚስትሪ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ እንዲሁም የሁለተኛ ዲግሪያቸውን በአናሊቲካል ኬሚስትሪ ከእንግሊዙ ኢስት አንግሊያ ዩኒቨርሲቲ 1980 . አግኝተዋል።

በኢትዮጵያ ጂኦሎጂካል ሰርቬይ በተለያዩ የኃላፊነት እርከኖች ሴቶችን ወክለው በላቀ አመራር አገልግለዋል፡፡ 1990 . የማዕድን እና ኢነርጂ ምክትል ሚኒስትር፣ 1994 . የማዕድን እና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታ፣ እንዲሁም 2002 . የማዕድን ሚኒስትር በመሆን ሀገራቸውን በከፍተኛ ታማኝነት አገልግለዋል።

በማዕድን እና ኢነርጂ ሚኒስቴር ቆይታቸው የኢትዮጵያን የማዕድን ሀብት ልማት ከማጠናከር ባሻገር፤ በጊቤ 1 እና 2 ጢስ ዓባይ 1 እና 2 ተከዜ፣ ፊንጫ አመርቲነሼ እና ጣና በለስ የኃይል ማመንጫዎች ግንባታ ጉልህ አሻራ አሳርፈዋል።

በተለይም ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ጥናት ተጠናቅቆ ወደ ግንባታ እንዲገባ እና በመጀመሪያዎቹ ዓመታት የግንባታ ክትትል ላይ የማይተካ ሚና ተጫውተዋል።

2006 እስከ 2010 . በብራዚል፣ አርጀንቲና እና ቺሊ የኢትዮጵያ ልዩ ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደር በመሆን የሀገራቸውን ብሔራዊ ጥቅም አስጠብቀዋል።

ከዚህም በተጨማሪ በኢትዮጵያ አየር መንገድ የዳይሬክተሮች ቦርድ አባልነት (የቪዥን 2025 ዕቅድን በማርቀቅ) በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ኮርፖሬሽን፣ በኢትዮጵያ ልማት ባንክ፣ በተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች እንዲሁም በሌሎችም በርካታ ሀገራዊ ተቋማት ላይ በቦርድ ሰብሳቢነት እና አባልነት በብቃት መርተዋል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል በመሆንም አገልግለዋል።

በሳይንስ፣ በምህንድስና፣ በመንግሥት አስተዳደር እና በዲፕሎማሲ ዘርፍ ለሚሠሩ ወጣቶች በተለይም ለሴቶች ትልቅ ተምሳሌት የነበሩት አምባሳደር ስንቅነሽ፤ የሁለት ልጆች እና የአንድ የልጅ ልጅ እናት ነበሩ።

የአምባሳደር ስንቅነሽ የቀብር ሥነ-ሥርዓት  ነገ በአዲስ አበባ ገርጂ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን ከቀኑ 6 ሰዓት ላይ እንደሚፈጸም ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ለኢቢሲ በላከው መግለጫ ተመላክቷል።

የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ለአምባሳደር ስንቅነሽ እጅጉ ቤተሰቦች፣ ወዳጅ ዘመዶች እንዲሁም የሥራ አጋሮች ጽናናትን ይመኛል።

አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: