የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርዓያ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ያለውን የምክክር ጉባኤ ሂደት አስመልክተው ማብራሪያ ሰጥተዋል።
በማብራሪያቸውም ተሳታፊዎች በ10 እና በ50 ንዑስ ቡድኖች ተከፋፍለው ሲወያዩባቸው የነበሩ ጉዳዮችን 250 አባላት ላለው ቡድን ሲያቀርቡ መቆየታቸውን ተናግረዋል።
በእነዚህ ውይይቶች መግባባት የተደረሰባቸው አጀንዳዎች በቀጣይ 500 አባላት ላሉት ጉባኤ እንደሚቀርቡ አስታውቀዋል።
ይህ የ500 አባላት ስብስብም በቀረቡለት አጀንዳዎች ላይ በስፋት ተወያይቶ ሐሳቦቹን የጋራ ካደረገ በኋላ ጉዳዮቹ ለዋናው ጠቅላላ ቡድን የሚቀርቡ ይሆናል ብለዋል።
በውይይቱ ሂደት በሐሳቦች ላይ ሙሉ በሙሉ መግባባት ላይ በማይደረስበት ጊዜ፣ ሁሉም ቡድኖች መርጠው ባዘጋጁዋቸው ቡድኖች አማካኝነት ተጨማሪ ውይይት እንደሚደረግባቸውም ፕሮፌሰር መስፍን አብራርተዋል።
ይህንን ተግባር የሚያከናውኑ 350 የሚሆኑ ተወካዮች ዛሬ የተመረጡ ሲሆን፣ እነዚህ ተወካዮች የቀረቡት ቃለ ጉባኤዎች ትክክለኛ መሆናቸውን በማረጋገጥ ይፈራረማሉ።
ተወካዮቹ የሚያጸድቋቸው እና የሚፈራረሙባቸው ሰነዶችም በቀጣዩ ሰኞ ጀምሮ ለጠቅላላው ጉባኤ እንደሚቀርቡ ተገልጿል።
በጉባኤው እየተከናወነ ያለው የተወካዮች ምርጫም ሆነ በውይይት አጀንዳዎቹ ላይ የሚደረገው መመካከር ያለምንም የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ ጣልቃ ገብነት ሙሉ በሙሉ በነጻነት እየተካሄደ መሆኑን ዋና ኮሚሽነሩ አረጋግጠዋል።
በለሚ ታደሰ
አስተያየትዎን እዚህ ያስፍሩ: